በወንጀል ተከሳሽ የሆነው ግለሰብ በቀጠሮው ቀን ባለመቅረቡ ዋሱ በፍርድ ቤቱ ተጠርቶ ይመጣል፡፡ በስራ ብዛት ይሁን በሌላ ምክንያት በፊታቸው ላይ መሰላቸት ጎልቶ የሚታባቸው ዳኛ ፊት ለፊታቸው የቆመውን ዋስ ስሙን ይጠይቁታል፡፡ ዋስ ስሙን ተናገረ፡፡ መፍረድ ብቻ ሳይሆን ማረጋገጥም የዳኞች ስራና ግዴታ ነውና እኚህ ዳኛም ማንነትህን እንዴት ማረጋገጥ እችላለሁ? መታወቂያ አለህ? ሲሉ ዋሱን ያፋጡታል፡፡
ዋሱ መታወቂያውን ረስቶ ኖሮ “የተከበረው ፍርድ ቤት ለጊዜው አልያዝኩትም” በማለት በእርጋታ መለሰ፡፡ “እና አንተነትህን እንዴት ማረጋገጥ እችላለሁ?” ዳኛው ኮስተር እያሉ መጡ፡፡ ሆኖም የዋሱን ግራ መጋባት በመመልከት ሌላ አማራጭ ፈለጉና “እሺ በዚህ ችሎት ውስጥ አንተን የሚያውቅ ምስክር መጥራት ትችላለህ?” ሲሉት ዋሱም “አዎ!” በማለት በችሎት ወደ ተኮለኮሉት ባለጉዳዮች ማተር ማተር አድርጎ አንድ በቅርበት የሚውቀውን የሰፈሩን ልጅ በማግኘቱ ደስ ብሎት “እሱ!” ብሎ ለዳኛው ጠቆማቸው፡፡ ዋሱ ምስክር ይሆነኛል ብሎ የቆጠረው ሰው ሰውነቱ ኮሳሳ ቢጤ ነበረ፡፡ ይሄ ነገር ለዳኛው ምቾት አልሰጣቸውም፡፡ እና ልክ ከመቀመጫው ብድግ እንዳለ ድሮም ተጨማዶ የነበረው ፊታቸው የባሰ በመጨማደድ “ቁጭ በይ! ደሞ አንቺን ብሎ ምስክር!” ብለው ቀልቡን ገፈው በሐፍረት እንዲቀመጥ አደረጉት፡፡ “ሌላ ሰው ጥራ!” ዳኛው ዋሱን እየገላመጡና ዝቅ ከፍ እያደረጉ አንባረቁበት፡፡
ሆኖም በችሎቱ ውስጥ ዋሱን አውቀዋለሁ የሚል ሰው ጠፋ፡፡ ስለሆነም የቀረው አንድ አማራጭ ከችሎት ወጥቶ ከመንገድ ዳር ሌላ ሰው መጥራት ብቻ ሆኖ ተገኘ፡፡ በዚሁ መሠረት ዋስ በፖሊስ አጃቢነት ወጥቶ አስፓልት ዳር ቆሞ ወጪ ወራጁን ሲያማትር በአጋጣሚ በጣም የሚያውቀውን ጓደኛውን አገኘ፡፡
በእፎይታ ስሜት እቅፍ አድርጎ ከሳመው በኋላ “እስኪ ባክህን አንድ ጊዜ.. ” ብሎ ጉዳዩን በማስረዳት እንዲተባበረው ይጠይቀዋል፡፡ አዲሱ ምስክር ትንሽ ለማቅማማት ቢዳዳውም ፖሊሱን ሲያይ ወደችሎት መግባቱ በግድም ቢሆን እንደማይቀርለት ስለተረዳ ምስክርነቱን ለመስጠት ወደ ፍርድ ቤቱ ዘው ብሎ ዳኛው ፊት ተገትሮ ይቆማል፡፡ መቼም ቢሆን በምንም ነገር የሚረኩ የማይመስሉት ዳኛ አሁንም ፊታቸውን አጨማድደው ወደ ዋሱ እያፋጠጡ “እህ ከየት ነው ያመጣኸው?” ሲሉ ይጠይቁታል፡፡ ዋሱ እጂን ወደ ላይ አንስቶ ጣቱን ወደ ዳኛው አቅጣጫ በመቀሰር “ከዛጋ!” ብሎ ገና መናገር እንደጀመረ ዳኛው “እህ ነይ ንኪኛ! ኧረ ንኪኝ!” በማለት ግራ አጋቡት፡፡ ዋሱም የተደበላለቀ የግርታ ስሜት ፊቱ ላይ እየተነበበት የቀሰረውን እጅ ሳያወርድ “እኮ ከዛ ጋ ነዋ!” ብሎ ወደ ግድግዳው አጠገብ ሲጠቁም ዳኛው አሁንም “ግድግዳውን ብሳዋ! ብሳው እንጂ!” በማለት ዋስና ምስክሩን ብቻ ሳይሆን በችሎት የነበረውን ባለጉዳይ ሁሉ ግራ አጋብተውታል፡፡ ለመሆኑ እኚህ ዳኛ ከሚስታቸው ጋር እንዴት ይሆን የሚግባቡት እንዴት ይሆን፡፡