የአሠሪና ሠራተኛ ህግ በዓለም ዓቀፍ ድርጅቶች እና የውጭ ዲፕሎማቲክ ሚሲዮኖች ላይ ያለው ተፈጻሚነት

መግቢያ

የአንቀጽ 3(3) ሀ ድንጋጌ ይዘት በሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ወይም ኢትዮጵያ በምትፈራረማቸው ዓለም አቀፍ ስምምነቶች አዋጁ ተፈፃሚ እንዳይሆን ሊወሰን እንደሚችል ይናገራል። ድንጋጌው በራሱ በግልጽ ወይም በተዘዋዋሪ የሚያገለው ሠራተኛ የለም። እስካሁን ድረስ ምክር ቤቱ በተሰጠው ስልጣን ተጠቅሞ ያወጣው ማግለያ ደንብ ካለመኖሩም በላይ የህጉ ተፈጻሚነት ወሰን በዓለም ዓቀፍ ስምምነቶች አልተገደበም።

የአሠሪና ሠራተኛ አዋጁ በዓለም ዓቀፍ ድርጅቶችና የውጭ ዲፕሎማቲክ ሚሲዮኖች ላይ ያለውን ተፈጻሚነት በማስቀረት ረገድ ‘ያለመከሰስ መብት’ (immunity) ቀዳሚውን ቦታ ይይዛል። ይህንን ከለላ አልፈው ወደ መደበኛው የክርክር ሂደት የሚዘልቁ ጉዳዮች ኢምንት ናቸው። ስለሆነም ከመነሻው አዋጁ በእነዚህ ድርጅቶችና ሚሲዮኖች ላይ ተፈጻሚ የሚሆንበት አጋጣሚ በጣም ጠባብ ከመሆኑ የተነሳ በአንቀጽ 3(3) ሀ እንደተመለከተው አዋጁ ተፈጻሚ እንዳይሆን ዓለም ዓቀፍ ስምምነት መፈረም ወይም በሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ማውጣት አስፈላጊ አይሆንም።

የሁለትዮሽ ወይም ዓለም ዓቀፍ ስምምነት አስፈላጊ የሚሆነው ከክስ ከለላ ለመስጠት ነው። ያለመከሰስ መብት የሚያጎናጽፍ የሁለትዮሽ ስምምነት የአገሪቱን ፍርድ ቤቶች የዳኝነት ስልጣን ያሳጣቸዋል። ስለሆነም ኢትዮጵያ ውስጥ ቅርንጫፍ ከፍቶ የሚንቀሳቀስ አህጉራዊ ወይም ዓለም ዓቀፋዊ ድርጅት በፍትሐ ብሔር ሆነ በወንጀል ከመከሰስ ከላለ የሚሰጥ በዋናው ድርጅትና በኢትዮጵያ መካከል የተፈረመ የሁለትዮሽ ስምምነት ካለ የድርጅቱ ሠራተኞች በኢትዮጵያ ፍርድ ቤቶች የሥራ ክርክር ማቅረብ አይችሉም። (አመልካች አቶ አለማየሁ መኮን እና ተጠሪ የምስራቅ አፍሪካ የበረሀ አንበጣ መከላከያ ድርጅት ታህሳስ 21 ቀን 2008 ዓ.ም. ሰ/መ/ቁ 117390 ቅጽ 19)

የዓለም ዓቀፍ ድርጅቶችና የውጭ ዲፕሎማቲክ ሚሲዮኖች ያለ መከሰስ መብት መርሆችና እሴቶች መሰረታቸው የተጣለው በጊዜ ሂደት ዳብረው ዓለም ዓቀፋዊ ተቀባይነት ባገኙ ገዢ ደንቦች ሲሆን እነዚህም ‘ልማዳዊ የዓለም ዓቀፍ ህግ’ (Customary International Law) ተብሎ በሚጠራው የህግ ክፍል ውስጥ ተጠቃለው ይገኛሉ። ያለ መከሰስ መብትን የሚመለከቱ አብዛኛዎቹ ደንቦች በጊዜ ሂደት በዓለም ዓቀፍ ስምምነቶች ቢተኩም በስምምነቶቹ ባልተሸፈኑ ጉዳዮች አሁንም ድረስ ልማዳዊ ዓለም ዓቀፍ ህግ ተፈጻሚነት አለው። እዚህ ላይ ያለ መከሰስ መብት ሲባል በማናቸውም ሁኔታ ቢሆን በእነዚህ ድርጅቶችና ተቋማት ላይ ክስ ለማቅረብ በሩ ሙሉ በሙሉ ዝግ ነው ማለት አይደለም። በጣም ጠባብ በሆኑ ሁኔታዎች ያለ መከሰስ መብት መከላከያ አይሆንም። የእነዚህ ሁኔታዎች ዝርዝር አፈጻጸም ከዚህ መጽሐፍ ወሰን ውጪ በመሆኑ የአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይን ጨምሮ በሌሎች ዓይነት ግንኙነቶች ላይ ያለ መከሰስ መብትን አስመልክቶ የወጡትን ዓለም ዓቀፍ ስምምነቶች ጠቅለል ባለ መልኩ እናያለን።

ዓለም ዓቀፍ ድርጅቶች

ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት ከክስ ከለላ የሚሰጥ ዓለም ዓቀፍ ስምምነት የወጣው እ.ኤ.አ. በ1946 ዓ.ም. ነው። Conventioncc on the Privileges and Immunities of the United Nations በሚል ስያሜ የሚታወቀው ይኸው ስምምነት በአንቀጽ 2 በክፍል ሁለት ላይ የድርጅቱን ያለ መከሰስ መብት እንደሚከተለው ይደነግጋል።

The United Nations, its property and assets wherever located and by whomsoever held, shall enjoy immunity from every form of legal process except insofar as in any particular case it has expressly waived its immunity shall extend to any particular case it has expressly waived its immunity. It is, however, understood that no waiver of immunity shall extend to any measure of execution.

በእርግጥ ከዚህ ስምምነት መውጣት ቀደም ብሎ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ቻርተር (UN Charter) ለድርጅቱ ያለ መከሰስ መብትና ልዩ መብቶች (privileges) ዕውቅና ሰጥቷል። እነዚህን መብቶች የሚያጎናጽፈው የቻርተሩ አንቀጽ 105 በይዘቱ ጠቅለል ያለ (ዝርዝር የአፈጻጸም ጉዳዮችን ያልያዘ) ሲሆን ያለ መከሰስ መብትን ከድርጅቱ ዓላማና ተግባር ጋር ያስተሳስረዋል።[1] ዓለም ዓቀፍ ስምምነቱ የቻርተሩ አንቀጽ 105 ዝርዝር ማስፈጸሚያ ተደርጎ ይወሰዳል።[2] በተባበሩት መንግስታት ድርጅት ስር የሚገኙት የተለያዩ ዓለም ዓቀፍ ተቋማት እንደ እናት ድርጅታቸው ሁሉ ያለመከሰስ መብት ያላቸው ሲሆን እ.ኤ.አ. በ1947 ዓ.ም. የወጣው Convention on the Privileges and Immunities of the Specialized Agencies በየአገራቱ በሚገኙ ፍርድ ቤቶች እንዳይከሰሱ ከለላ ይሰጣቸዋል።

ዲፕሎማቲክ ሚሲዮኖች

የውጭ አገር ዲፕሎማቲክ ሚሲዮኖች ሲባል ኤምባሲ፣ ቋሚ መልዕክተኛ ጽሕፈት ቤት፣ ቆንሲላ ጽሕፈት ቤት፣ የክብር ቆንሲላ ጽሕፈት ቤት እና የመሳሰሉትን ያጠቃልላል። እነዚህ የአንዲት ሉዓላዊት አገር ወኪሎች ናቸው። ያለ መከሰስ መብቱ የሚሰጠው ለወከሉት አገር ነው። ልማዳዊ ዓለም ዓቀፍ ህግ (Customary International Law) ሙሉ በሙሉ የንግድ ጠባይ ያላቸው ግንኙነቶች ብሎም በግል የሚፈጸሙ ተግባራትን ከአገራዊ፣ ሉዓላዊ ወይም መንግስታዊ ተግባራት ይለያል።[3] አገራት ያለመከሰስ መብት የሚኖራቸው በሁለተኛዎቹ ዓይነት ተግባራት ነው።[4] የአገራት (ስለሆነም ዲፕሎማቲክ ሚሲዮኖች) ያለመከሰስ መብት በተመለከተ ተፈጻሚነት ያለው ዓለም ዓቀፍ ስምምነት እ.ኤ.አ. በ2004 ዓ.ም. የወጣው United Nations Convention on Jurisdictional Immunities of States and Their Property ሲሆን ያለመከሰስ መብትን አስመልክቶ ካቀፋቸው ጠቅለል ያሉ ድንጋጌዎች በተጨማሪ በቅጥር ግኝኑነት ወቅት የመብቱን አፈጻጸም የሚወሰን ልዩ ድንጋጌ ይዟል።[5]

የፍርድ አፈጻጸም

ዓለም ዓቀፍ ድርጅቶችና ዲፕሎማቲክ ሚሲዮኖች በራሳቸው ፈቃድ (waiver) ወይም ያለመከሰስ ከለላቸው ተፈጻሚ በማይሆንባቸው ጠባብ ሁኔታዎች አንድ ፍ/ቤት በዋናው ጉዳይ ላይ አከራክሮ ውሳኔ መስጠቱ ውሳኔውን ወዲያውኑ ተፈጻሚ አያደርገውም። የክስ ከለላ (Immunity from Suit) እና የአፈጻጸም ከለላ (Immunity from Execution) ሁለቱም የሚታዩት በተናጠል ነው። ከላይ በተጠቀሱት ዓለም ዓቀፍ ስምምነቶች ብሎም ሰፊ ተቀባይነት ባገኙት የልማዳዊ ዓለም ዓቀፍ ህግ መርሆዎች መሰረት የተለያዩ ቅድመ ሁኔታዎችና መለኪያዎች መሟላታቸው ሳይረጋገጥ በእነዚህ አካላት ላይ የተሰጠ ፍርድ አይፈጸምም። ለምሳሌ ድርጅቶቹ ለዓላማቸው ማስፈጸሚያ አስፈላጊ በሆነ ንብረት ላይ አፈጻጸም ሊቀጥል አይችልም። ከዚህ በተጨማሪ ፍርድ የተሰጠው ያለመከሰስ መብትን የሚመለከቱ የዓለም ዓቀፍ ህጎችንና ስምምነቶችን በመጣስ ከሆነ በአፈጻጸም ተግባራዊ የሚደረግበት አግባብ አይኖርም።

ከአፈጻጸም ከለላ ጋር በተያያዘ በሰበር ችሎት በታየ አንድ የሥራ ክርክር መዝገብ (አመልካች አቶ አለማየሁ ኦላና እና ተጠሪ የተባበሩት መንግስታት የልማት ድርጅት (UNDP) ህዳር 10 ቀን 2007 ዓ.ም. ሰ/መ/ቁ 98541 ቅጽ 17) ተጠሪ በሌለበት የተሰጠውን ፍርድ ለማስፈጸም የቀረበ ጥያቄ ውድቅ ተደርጓል። ተጠሪ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት ስር የሚገኝ ዓለም ዓቀፍ ተቋም ነው። ያለመከሰስ መብትን አስመልክቶ በወጣው ኮንቬንሽን (Convention on the Privileges and Immunities of the Specialized Agencies) አንቀጽ 3 ክፍል 3 እና 4 መሰረት ተቋማቱ በክስ ሆነ በአፈጻጸም በፍ/ቤት ቀርበው እንዳይጠየቁ ከለላ ተሰጥቷቸዋል። ስለሆነም የፍርዱ ፍሬ በአፈጻጸም መነፈጉ ከስምምነቱ ድንጋጌዎች ጋር ይጣጣማል። ያም ሆኖ ግን በሰ/መ/ቁ 98541 የአፈጻጸም ጥያቄውን ላለመቀበል መነሻ የሆነው ምክንያት የአፈጻጸም ከለላ መሰረተ ሓሳብ ሳይሆን የአዋጁ አንቀጽ 3(3) ሀ ድንጋጌ ነው። ይሁን እንጂ የአንቀጽ 3(3) ሀ ድንጋጌ የአሠሪና ሠራተኛ አዋጁ በዓለም ዓቀፍ ድርጅቶችና ዲፕሎማቲክ ሚሲዮኖች ላይ ተፈጻሚ ላይሆን የሚችልበትን ሁኔታ ከመጠቆም ውጪ ተፈጻሚነቱን በቀጥታ ወይም በተዘዋዋሪ አያገልም። ይህን አስመለክቶ ኢትዮጵያ የፈረመቸው ስምምነት ሆነ በሚኒስትሮች ምክር ቤት የወጣ ደንብ የለም። በተጨማሪም የድንጋጌው ግልጋሎት ከፍርድ በፊት እንጂ በኋላ አይደለም። የድንጋጌውን ትክክለኛ ይዘት ለመረዳት ሁለቱም ነጥቦች ጠቃሚ ቢሆኑም አዋጁ በተጠቀሱት ድርጅቶች ላይ ያለውን ተፈጻሚነት ለመወሰን አስፈላጊ አይደሉም። ያለመከሰስ መብት መልስ ሳያገኝ ስለ አንቀጽ 3(3) ሀ አይወራም። አዋጁን ተንተርሶ የሚቀርብ የሥራ ክርክር ክስ በድርጅቶቹ ያለመከሰስ መብት የተነሳ ውድቅ መደረጉ ስለማይቀር በድንጋጌው የሚመለስ ጭብጥ አይኖርም።


[1] C. F. Amerasinghe, Principles of the institutional law of international organizations (2nd Rev. New York: Cambridge University Press, 2005) ገፅ 317-8

[2] ዝኒ ከማሁ ገፅ 318

[3] Xiaodong Yang, State Immunity in International Law (Cambridge University Press, 2012) ገፅ 34

[4] ዝኒ ከማሁ

[5] ዝኒ ከማሁ በጉዳዩ ላይ ጠለቅ ያለ ማብራሪያ ለማግኘት በቅጥር ግንኙነት ወቅት ያለ መከሰስ መብትን ከቅጥር ግኝኑነት ጋር በተያያዘ በስፋት የተዳሰሰበትን የመጽሐፉን ምዕራፍ 4 (ገፅ 132-198) ይመልከቱ፡፡

የአሠሪና ሠራተኛ ህግ እና የውል ህግ ተዛምዶ

የአሠሪና ሠራተኛ ህግ እና የውል ህግ

የአሠሪና ሠራተኛ ህግ የሥራ ውል እንደመሆኑ ለውል ህግ መሰረታዊ ደንቦች ይገዛል። ስምምነቱ በህግ ማዕቀፍ የሥራ ውል ተብሎ በሚጠራው የውል ዓይነት አማካይነት መልክ ይዞ ይቀረጻል። የሥራ ውል እንደማንኛውም ዓይነት ውል ሁሉ ለውል ህግ መሰረታዊ መርሆዎችና ደንቦች ተገዢ ነው። በፍ/ህ/ቁ 1676(1) ግልጽ ሆኖ እንደተደነገገው ውሎች ዓይነታቸው ሆነ ምክንያታቸው ማንኛውም ቢሆን በውል ህግ ጠቅላላ ደንቦች ይመራሉ። የሥራ ውል ሲመሰረት የሠራተኛው ሥራ የመሥራት፤ የአሠሪው ደመወዝ የመክፈል ግዴታዎች የተዋዋይ ወገኖች ተቀዳሚ ግዴታዎች ናቸው። በግላዊ የቅጥር ግንኙነት ውስጥ የሥራ ውል የሚጫወተውን ዓይነተኛ ሚና እንዲሁም በግዴታዎቹ መካከል ያለውን ትስስር የሰበር ችሎት በሰ/መ/ቁ 17189 (አመልካች የሸቀጦች ጅምላ ንግድና አስመጪ ድርጅት እና ተጠሪ አቶ ንጉሴ ዘለቀ ጥቅምት 17 ቀን 1998 ዓ.ም. ቅጽ 2) ሰፋ ያለ ትንተና በመስጠት እንደሚከተለው ገልጾታል።

“የሠራተኛና የአሠሪ ግንኙነት የሚመነጨው ሁለቱም ወገን ከሚገቡት ውል ነው። ይኸው ውል እንደማንኛውም ሌላ ውል ለሁለቱም ወገን መብት ያመነጫል ግዴታንም ይጥላል። ከነዚህ ተያያዥ መብትና ግዴታዎች አንዱ ሠራተኛው በውል ለማከናወን ቃል የገባውን ሥራ የማከናወን በተሠራው ሥራ መጠን ደግሞ በውሉ በተጠቀሰው ጊዜና መጠን ደመወዝ የማግኘት መብትና ግዴታ ነው። በዚህ መሠረት አሠሪው ከሠራተኛው ግልጋሎት ያገኛል። ባገኘው ግልጋሎት መጠንም በውሉ የተጠቀሰውን ደመወዝ የመክፈል ግዴታ ይኖርበታል። በመርህ ደረጃ እነዚህ መብትና ግዴታዎች ከውል የሚመነጩ አንዱ ያለሌላው ሊታሰቡ የማይችሉ የአንድ ሕጋዊ ግንኙነት ሁለት ገጽታዎች ናቸው።”

የችሎቱ ትንተና የአሠሪና ሠራተኛ ህግ ያልሸፈናቸው ጉዳዮች ሲያጋጥሙ መፍትሔ ፍለጋ ወደ ውል ህግ ድንጋጌዎች መሄድ እንደሚገባ ጠቃሚ ቁምነገር ያስጨብጠናል። ቁምነገሩ ግን ሌላ ጠቃሚ ቁምነገር ይወልዳል፤ ይኸውም ወደ ውል ህግ ከማማተር በፊት በቅድሚያ የአሠሪና ሠራተኛ ህጉን ‘አሟጦ’ ለመተርጎም መሞከርና በትርጉም የማይደፈን ቀዳዳ መኖሩ ማረጋገጥ ይገባል። በተጠቀሰው መዝገብ ወደ ውል ህግ ትንተና የተገባው የአሠሪና ሠራተኛ አዋጅ ፀንቶ በነበረበት ጊዜ የሥራ ውል ከህግ ውጭ ሲቋረጥ የውዝፍ ደመወዝ አከፋፈልን ለመወሰን ነው። ለዚህ ደግሞ ህጉ ራሱ በቂ ምላሽ ነበረው። ‘ወደ ሥራ መመለስ’ ከእንግሊዝኛ አቻው reinstatement ጋር ከተገናዘበ በህገ-ወጥ መንገድ የተሰናበተ ሠራተኛ ወደ ሥራ እንዲመለስ /reinstated/ ሲወሰንለት የሚመለሰው ባዶ እጁን ስላለመሆኑ የእንግሊዝኛውን ቃል ጽንሰ ሀሳብ መረዳት ብቻውን ይበቃል።

የችሎቱ ትንተና አግባብነት ትንተና በተሰጠበት በዛው መዝገብ ሳይሆን በሰ/መ/ቁ 03171 (አመልካች የኢት/ኤሌክትሪክ ኃ/ኮርፖሬሽን እና ተጠሪ ወ/ት ትርሲት ደገፉ ህዳር 16 ቀን 2001 ዓ.ም ቅጽ 8) ጎልቶ ይታያል። በዚህ መዝገብ የሥራ ውል የሚመሰረትበት ጊዜ አከራካሪ ጭብጥ ነበር። የሥራ ውል አለ የሚባለው ሠራተኛው ሥራውን ከጀመረበት ጊዜ ነው? ወይስ የቅጥር ደብዳቤ ከተሰጠበት ጊዜ ጀምሮ? አሠሪና ሠራተኛ ህግ ቦታውን ለውል ህግ ካላስረከበ በቀር ጥያቄው አይመለስም። የሰበር ችሎት በውል ህግ የውል አቀራረብ እና አቀባበል የሚመሩባቸውን ድንጋጌዎች ወደ ሥራ ውል በማምጣት የሥራ ውል ተመስርቷል የሚባለው ሠራተኛው ሥራ ሲጀምር ሳይሆን የቅጥር ደብዳቤ ሲቀበል እንደሆነ በማተት የአዋጁ ክፍተት እንዲሞላ አድርጓል።

የውል ህግን ፋይዳ ለማጉላት ተጨማሪ አስረጂ ምሳሌዎች መጥቀስ ይቻላል። በአዋጁ አንቀጽ 36-38 አሠሪው ደመወዝን ጨምሮ ሌሎች ክፍያዎች በሰባት ቀናት ውስጥ ለመክፈል የሚገደደው፤ ግዴታውን ጥሶ ክፍያ ካዘገየም ቅጣት የሚከፍለው የሥራ ውሉ ሲቋረጥ ነው። የሥራ ውል ፀንቶ ባለበት ጊዜ የደመወዝ ክፍያ በመዘግየቱ የተነሳ በሠራተኛው ላይ ለሚደርሰው ጉዳት ህጉ መፍትሔ አላበጀለትም። እንበልና ለስድስት ወር ደመወዝ ያልተከፈለው ሠራተኛ በፍርድ ቤት ክስ ቢመሰርት ከረጅም ጊዜ ክርክር በኋላ ካልተከፈለው ደመወዝ ውጭ ሌላ ዳኝነት አያገኝም። ምክንያቱም የአሠሪና ሠራተኛ ህጉ የሥራ ውል ሲቋረጥ እንጂ ፀንቶ ባለበት ጊዜ ለመደመዝ ክፍያ በቂ አስተማማኝ ጥበቃ ማድረግ ተስኖታል። ይሄን የህጉን ድክመት ማረም የሚቻለው በመደበኛው የውል ህግ ድንጋጌዎች ነው። ደመወዝ መክፈል ዓይነተኛ የአሠሪ ግዴታ እንደመሆኑ ይሄን ግዴታውን የጣሰ አሠሪ በውል መጣስ ሠራተኛው ላይ ላደረሰው ጉዳት ተጠያቂ ይሆናል። ደመወዝ ማዘግየት ውል መጣስ እንደመሆኑ ሠራተኛው የደረሰበት ጉዳት በውል ህግ ድንጋጌዎች ተመዝኖ ይካሳል።

ከአሠሪና ሠራተኛ ህግ የሚመመዘዙ ጥያቄዎችን ለመፍታት የውል ህግ ተገቢ የሚሆንባቸው ሌሎች ሁኔታዎች /ከሥራ ውል መቋረጥ ጋር በተያያዘ/ በዚህ መጽሐፍ ምዕራፍ 6 (6.5 በአዋጁ ያልተካተቱ ጉዳዮች) በሚለው ክፍል ስር የተዳሰሱ በመሆኑ ለበለጠ ግንዛቤ አንባቢ እንዲመለከተው ይመከራል።

የውል ህግ ‘ክፍተት የመሙላት’ ሚና ከአሠሪና ሠራተኛ ህግ መሰረታዊ ዓላማ ጋር መናበብ ይኖርበታል። ለምሳሌ የፀና ውል እንዲኖር በውል ህግ አንቀጽ 1678 ከተጠቀሱት መካከል የተዋዋይ ወገኖች ፈቃድ እና የውሉ ህጋዊነት በተመሳሳይ ለሥራ ውልም ተፈጻሚነት አላቸው። እንበልና አሠሪው ድርጅት የተቋቋመበት መንገድ ህገ-ወጥ ከሆነ የሥራ ውሉ ህጋዊነት ኖሮት ሊቀጥል አይችልም። በውል ህግ መነጽር ሲታይ እንዲህ ዓይነት ውል ዋጋ አልባ ቢሆንም የድርጅቱን ሠራተኞች ያልተከፈለ ደመወዝ እና ሌሎች ክፍያዎች የማሳጣት ውጤት ሊኖረው አይገባም።

ህጋዊ እና ህገ-ወጥ የሥራ ውል መታገድ ውጤት

የሥራ ውል መታገድ

የህጋዊ ዕገዳ ውጤት

በህጉ ላይ በተዘረዘሩት አጥጋቢ ምክንያቶች የተነሳ ከሥራ ውል የሚመነጩ መብትና ግዴታዎች ለጊዜው መታገድ የሠራተኛውን የመስራት ግዴታ እና የአሠሪውን ደመወዝ የመክፈል ግዴታ ለጊዜው ቀሪ ያደርጋል። ከላይ ለመጠቆም እንደተሞከረው ዕገዳ የሥራ ውሉን ለጊዜው የማቋረጥ ሆነ ቀሪ የማድረግ ውጤት ስለሌለው የአገልግሎት ዘመን አይቋረጥም። ስለሆነም የስንብት ክፍያ ለማስላት፣ የማስጠንቀቂያ ጊዜን ለመወሰን እንዲሁም የሥራ ልምድ የምስክር ወረቀት ለመስጠት ዕገዳው ጸንቶ የነበረበት ጊዜ ከሠራተኛው የአገልግሎት ዓመት ላይ ተቀናሽ ሊደረግ አይገባውም።

የዕገዳ ጊዜ ማብቃት

የዕገዳው ጊዜ ሲያበቃ ውጤቱም አብሮ ያበቃል። ማብቃቱን ተከትሎ ሠራተኛው በሚቀጥለው ቀን በሥራ ቦታው ላይ መገኘት አለበት። በአዋጅ ቁ. 377/96 አንቀጽ 22 የዕገዳ ጊዜው ሲያበቃ የአሠሪው ግዴታ ሠራተኛውን ወደ ሥራው እንዲመልሰው ግዴታ ጥሎበት ነበር።[1] ይህ አንቀጽ በአዋጅ ቁ. 1156/2011 ተሻሽሏል። በማሻሻያው መሰረት አሠሪው ሠራተኛውን የሚመልሰው ወደ ቀድሞ ሥራው ሳይሆን ሲከፈለው የነበረውን ደመወዙን በመጠበቅ ከሙያው ጋር አግባብነት ባለው የሥራ መደብ ላይ ነው። ይህ ለምን አስፈለገ? የአዋጁ ሐተታ ዘምክንያት እንደሚነግረን ማሻሻያው ያስፈለገበት ምክንያት የእገዳ ጊዜ ማብቃት ተከትሎ ሠራተኞች ወደ ስራ ሲመለሱ ከምደባ ጋር ተያይዞ እየተነሱ ያሉ የስራ ክርክሮች መፍትሄ ለመስጠት እንዲቻል ነው።

የዕገዳ እርምጃ መነሻ ምክንያት የድርጅቱን ሥራ በከፊል የሚቀንስ ወይም በሙሉ የሚያስቆም ያልተጠበቀና ከአቅም በላይ የሆነ ምክንያት ነው። ሠራተኛው ሲታገድ የሥራ መደቡም ክፍት ሆኖ ይቆያል። የዕገዳ ጊዜው ሲያበቃ ሠራተኛው ክፍት ሆኖ በሚቆየው የሥራ መደቡ ላይ ይመለሳል። ስለሆነም ዕገዳ በባህርዩ ከምደባ ጋር ተያይዞ የሚያስነሳው የሥራ ክርክር የለም። ክርክር ሊነሳ የሚችለው በታገዱት ሠራተኞች የሥራ መደብ ላይ አሠሪው ሌሎች ሠራተኞች የቀጠረ እንደሆነ ነው። ይህ ደግሞ ዓይን ያወጣ ህገ-ወጥነት ነው። ድርጅቱ ሌሎች ሠራተኞችን የሚያስቀጥር ሥራ ከነበረው ከመሻው የዕገዳ እርምጃ የተወሰደው ለዕገዳ የሚያበቃ እውነተኛና ተጨባጭ ምክንያት ባልነበረበት ሁኔታ እንደሆነ ያሳያል። ማሻሻያው በዕገዳ ስም የሚደረግን ህገ-ወጥ የምደባ ለውጥ ከመከላከል ይልቅ ህገ-ወጥነትን ያበረታታል።

የዕገዳ ምክንያት አለማብቃት

የዕገዳ ጊዜ ማብቃት የዕገዳ ምክንያት ማብቃትን አያሳይም። አሠሪውን የሚመለከቱ የማገድ ምክንያቶች አሠሪው ከተፈቀደለት ወይም በህጉ ከተቀመጠው የዘጠና ቀናት ጊዜ በላይ ሊዘልቁ ይችላሉ። ይህ ሲሆን የአዋጅ ቁ. 377/96 አንቀጽ 21(2) ሠራተኛውን የስንብት ክፍያ እና የማስጠንቀቂያ ጊዜ ክፍያ የማግኘት መብቱን ይጠብቅለታል። ክፍያዎቹ የሥራ ውል መቋረጥ ውጤቶች እንደመሆናቸው ውሉ የሚቋረጥበት መንገድ ሳይታወቅ ስለክፍያ ማውራት ከማደናገር የዘለለ ፋይዳ የለውም። የሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ከሚወስነው ወይም በህጉ ከተቀመጠው የዘጠና ቀናት ማብቃት በኋላ የዕገዳ ምክንያት አለማብቃት (መቀጠል) በራሱ የሥራ ውልን የሚያቋርጥ በቂ ምክንያት አይደለም። ይህ ፈጦ የወጣ የህጉ ግድፈት በማሻሻያው መስተካከል ቢኖርበትም ከመስተካከል ይልቅ ችግሩ ገዝፎ እንዲባባስ ተደርጓል።

አዋጅ ቁ. 1156/2011 በአንቀጽ 21(2) ላይ ‘ካመነ’ ከሚለው ቀጥሎ ‘ሠራተኛው የቅጥር ውሉ ተቋርጦ’ የሚል ሐረግ ጨምሮበታል። ‘ካመነ’ በሚል ልኩ የማይታወቅ ተለጣጭ ስልጣን (discretion) የሚያጎናጽፈው ማሻሻያ ስልጣኑ የተሰጠው አካል ይህን ስልጣን በመገልገል ስለሚሰወደው እርምጃ ወይም ውሳኔ በዝምታ አልፎታል። ‘ሠራተኛው በአንቀጽ 39 እና 44 የተመለከቱትን ጥቅሞች የማግኘት መብት አለው።’ የሚለው የቀድሞው አዋጅ ሆነ ‘ሠራተኛው የቅጥር ውሉ ተቋርጦ በአንቀጽ 39 እና 44 የተመለከቱትን ጥቅሞች የማግኘት መብት አለው።’ የሚለው አዲሱ አዋጅ ሁለቱም በውሉ ዕጣ ፈንታ ላይ ማን ወሳኝ እንደሚሆን ግልጽ አላደረጉትም። ውሉ የሚቋረጠው በህግ በተደነገገው መንገድ? በሚኒስቴሩ ወይም አግባብ ባለው ባለስልጣን ውሳኔ? ወይስ በአሠሪው አነሳሽነት?

ከሥራ ውል የሚመነጭ መብትና ግዴታ ለጊዜው መታገድና የዕገዳው ምክንያት አለማብቃት በቀጥታ ወደ ሥራ ውል መቋረጥ ያመራበት ምክንያት ሐተታ ዘምክንያቱ ሊመልሰው የሚገባ መሰረታዊ ጥያቄ ነበር። በመጀመሪያ ደረጃ አሠሪው ሥራውን እንደገና ለመቀጠል የማይችል ከሆነ በአንድ ተቋም ዕምነት ሳይሆን በተጨባጭ ማስረጃ ሊረጋገጥ ይገባል። ማረጋገጫ ከተገኘ ደግሞ የሥራ ውሉ ሊቋረጥ የሚችለው በአንቀጽ 24/4/ (ድርጅቱ በመዘጋቱ) ወይም በአሠሪው አነሳሽነት በአንቀጽ 28(2) ሀ (በቅነሳ) ነው። ዕገዳ መኖሩ የሁለቱን ድንጋጌዎች ተፈጻሚነት ሊያስቀር እንደማይገባ ግልጽ ነው። 

የዕገዳ ጊዜ ማብቃትን ተከትሎ አሠሪው ምን ማድረግ አለበት? ወይም ውሉን በየትኛው ድንጋጌ መሰረት ማቋረጥ አለበት? የሚለው ጥያቄ ሊያስጨንቅ የሚገባው አሠሪውን እንጂ አስፈጻሚውን አካል አይደለም። ለዕገዳው ምክንያት የሆነው ነገር ከዕገዳ ጊዜው በላይ ቢቀጥልም ባይቀጥልም የዕገዳ ምክንያት አለማብቃት ህጋዊ ውጤቱ በአንቀጽ 22 ላይ ከተቀመጠው ውጪ አይወጣም። የዕገዳ ጊዜው እስካበቃ ድረስ የዕገዳው ምክንያት አበቃም አላበቃም ለጊዜው ታግደው የነበሩት መብትና ግዴታዎች ውጤት ማግኘት ይጀምራሉ። ከዚህ በኋላ የሚሆነውን ‘ሚኒስቴሩ ወይም አግባብ ያለው ባለስልጣን ካመነ’ የሚወስነው አይደለም። ከዚያ ይልቅ ከዕገዳው ማብቃት በኋላ ከአቅም በላይ የሆነው ምክንያት ወይም ያልታሰበ የገንዘብ ችግር ካልተወገደ የመዋቅር ለውጥ ማድረግ፣ የቅነሳ እርምጃ መውሰድ፣ ድርጅቱን ሙሉ በሙሉ መዝጋት ብሎም መፍትሔ ሊሆን የሚችል የተለየ ዕቅድ መቀየስና መተግበር በአጠቃላይ የችግሩን ስፋትና ጥልቀት አይቶ ይበጀኛል የሚለውን መወሰን የአሠሪው ስልጣን ነው።

የህገ-ወጥ ዕገዳ ውጤት

ሠራተኛውን በሚመለከቱ ምክንያቶች የዕገዳው ምክንያት መኖር እንጂ ህጋዊነቱ ጥያቄ ሆኖ አይነሳም። በአንቀጽ 18 ንዑስ አንቀጽ 1 እስከ 4 በተመለከቱት ምክንያቶች ሠራተኛው ከሥራ ሲቀር በአሠሪው ከሚወሰድበት የስንብት እርምጃ ከለላ ያገኛል። በተጨማሪም ሥራውን በገዛ ፈቃዱ እንደለቀቀ ግምት እንዳይወሰድበት እነዚህን ምክንያቶች እንደ መከላከያ ሊያቀርባቸው ይችላል። ለመሆኑ ከሥራ ለመቅረቱ በቂ የዕገዳ ምክንያት እንደነበረው ማስረዳት የሚችለው እንዴት ነው?

በአንቀጽ 18(1) እና (2) ፈቃድ እንደተሰጠ መረጋገጥ ያለበት ሲሆን በንዑስ አንቀጽ 3 ደግሞ ሠራተኛው ታስሮ እንደነበረና የታሰረበት ጊዜም ከ30 ቀናት እንደማይበልጥ እንዲሁም መታሰሩ ለአሠሪው እንደተነገረው ወይም የሚያውቅበት መንገድ ስለመኖሩ መረጋገጥ ያለባቸው ጉዳዮች ናቸው። ብሔራዊ ጥሪን አስታኮ መከላከያ ለማቅረብ ከሥራ መቅረት በብሔራዊ ጥሪ ሳቢያ እንደተከሰተ ሊረጋገጥ ይገባል። ብሔራዊ ጥሪ የፍሬ ነገርና የሕግ ጉዳይ እንደመሆኑ ሠራተኛው የት እንደነበረ በማስረጃ ማረጋገጡ ብቻውን አይበቃም። በፍሬ ነገር የተረጋገጠው ምክንያት የብሔራዊ ጥሪን ትርጓሜ አሟልቶ መገኘት ይኖርበታል። እንበልና አንድ ሠራተኛ በጎርፍ ለተጠቁ ወገኖች እገዛ ለማድረግ በመሄዱ ለአንድ ወር ያህል ከሥራ ቀርቷል። የጎርፍ አደጋ መድረሱና ሠራተኛው አደጋው ቦታ ተገኝቶ አንድ ወር ሙሉ እርዳታ ሲያደርግ መቆየቱ በማስረጃ ከተረጋገጠ በኋላ ፍሬ ነገሩ ከብሔራዊ ጥሪ ትርጓሜ አንጻር ይመዘናል።

ብሔራዊ ጥሪ የሚለው ቃል ከ1983 ዓ.ም. ወዲህ በመንግስት ሆነ በማህበረሰቡ ዘንድ ጥቅም ላይ ሲውል አይታይም። ከዚህ አንጸር የቃሉን ትክክለኛ ይዘትና ወሰን እርግጠኛ ሆኖ መናገር ያስቸግራል። ሆኖም ቃሉ አገራዊና ይፋዊ መልክ የያዘ በመሆኑ ብሔራዊ ጥሪ ሲባል አገራዊ ችግር ሲከሰት ዜጎች መንግስት ባደረገላቸው ጥሪ መሰረት የበኩላቸውን እገዛ የሚያደርጉበት ክስተት ነው ማለት እንችላለን። ወሳኙ ነጥብ የተከሰተው ችግር ስፋትና ጥልቀት ሳይሆን በመንግስት በኩል ይፋዊ ጥሪ መኖሩ ነው። ስለሆነም በአንድ አካባቢ ላይ የጎርፍ አደጋ በመድረሱ ምክንያት እገዛ ለማድረግ በሚል ከሥራ መቅረት ብቻውን በብሔራዊ ጥሪ ውስጥ የሚወድቅ ምክንያት አይሆንም።

በአንቀጽ 18 ከንዑስ አንቀጽ 1 እስከ 4 የተመለከቱት በቂ ምክንያቶች ሳይኖሩ ሠራተኛው ከሥራ ከቀረ ካለበቂ ምክንያት ክሥራ እንደቀረ ስለሚቆጠር አሠሪው የሥራ ውሉን በአንቀጽ 27/1/ ለ በህጋዊ መንገድ ሊያቋርጠው ይችላል።

አሠሪውን በሚመለከቱ ምክንያቶች ከሥራ ውል የሚመነጩ መብትና ግዴታዎች ለጊዜው መታገድ መሰረታዊ የሆነውን የሠራተኛውን የመስራት እና ደመወዝ የማግኘት መብት አደጋ ውስጥ ይከታል። ሆኖም መታገዱን በመከልከል አደጋውን ማስቀረት አይቻልም። እንዲያውም እገዳ አስፈሪው የሠራተኞች ቅነሳ እንዳይኖር ተመራጭ መፍትሔ ነው። ህጉ እገዳን ማስቆም ባይችልም የስነ-ስርዓት ቅድመ ሁኔታዎችን በመዘርጋት ለሠራተኛው ጥበቃ ያደርጋል። ጥበቃው ከቅነሳ ጋር ሲነጻጸር ይበልጥ ጠንካራ ነው።

የቅነሳ እርምጃ ሲወሰድ ህጋዊ በቂ ምክንያቶች መኖራቸው የመወሰን ስልጣን ሙሉ በሙሉ ለአሠሪው የተተወ ነው። በተቃራኒው በአንቀጽ 18/1/ እና /2/ መሰረት የዕገዳ እርምጃ ሲወሰድ በድንጋጌዎቹ የተመለከቱት በቂ ምክንያቶች መኖራቸው የሚረጋገጠው በራሱ በአሠሪው ሳይሆን በሠራተኛ ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ወይም አግባብ ባለው ባለስልጣን ነው። አሠሪው የዕገዳ እርምጃ ሲወስድ የዕገዳውን ምክንያት ለሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ወይም አግባብ ላለው ባለስልጣን ካላስታወቀና ዕግዱ ካልፀደቀ እርምጃው ህጋዊ አይሆንም።

በአንቀጽ 18 (5) ወይም (6) በተመለከተው ምክንያት ከሥራ ውል የሚመነጩ መብትና ግዴታዎችን ለማገድ አሠሪው ለእገዳው ምክንያት የሆነው ሁኔታ ባጋጠመው በ3 የሥራ ቀናት ውስጥ ለሚኒስቴሩ ወይም አግባብ ላለው ባለስልጣን በጽሑፍ ማስታወቅ አለበት።[2] የግዴታው ዓይነት ሚኒስቴሩ ወይም አግባብ ያለው ባለስልጣን ጉዳዩን እንዲያውቀው ‘በጽሑፍ መንገር’ ቢመስልም በአንቀጽ 20 ውሳኔ ሰጭው አካል ከተሰጠው ስልጣን ይዘት አንጻር ሲታይ ‘ማስታወቅ’ የተባለው ፈቃድ ለማግኘት የሚቀርብ ማመልከቻ ነው። ምክንያቱም ሚኒስቴሩ ወይም አግባብ ያለው ባለስልጣን የጽሑፍ ማስታወቂያ በደረሰው በሦስት የሥራ ቀናት ውስጥ ለእገዳው በቂ ምክንያት ስለመኖሩ እንደሚወስን በድንጋጌው ላይ ተመልክቷል። በቂ ምክንያት ከሌለ ጥያቄው ተቀባይነት አላገኘም ማለት ነው። ሚኒስቴሩ እገዳውን ቢፈቅድም ሊቆይ የሚችለው ቢበዛ ለ90 ቀናት ነው።

ከሥራ ውል የሚመነጩ መብትና ግዴታዎችን የማገድ እርምጃ በሚከተሉት ሁኔታዎች ህገ-ወጥ ሊሰኝ ይችላል። እነዚህም የሚከተሉት ናቸው።

  1. የማስታወቅ ግዴታን መጣስ
  2. የሚኒስቴሩን ወይም አግባብ ያለው ባለስልጣን ውሳኔ መጣስ

የማስታወቅ ግዴታን መጣስ

አሠሪው ለእገዳው ምክንያት የሆነው ምክንያት ባጋጠመ በሶስት የሥራ ቀናት ውስጥ የጽሑፍ ማስታወቂያ እንዲሰጥ በህግ የተጣለበትን ግዴታ ወደ ጎን በማድረግ የሚወስደው የማገድ እርምጃ ህጋዊነት ይጎድለዋል። ከላይ ለመጠቆም እንደተሞከረው የማስታወቅ ግዴታ ዋና ዓላማው ከሥራ ውል የሚመነጩ መብትና ግዴታዎች መታገዳቸውን ለመንገር ሳይሆን በቅድሚያ ፈቃድ ለማግኘት ነው።

የባለስልጣኑን ውሳኔ መጣስ

ሚኒስቴሩ ወይም አግባብ ያለው ባለስልጣን ማስታወቂያ ሲደርሰው ሁለት ነገሮችን ይመረምራል። አንደኛ አሠሪው ያቀረበው ምክንያት በአንቀጽ 18/5/ ወይም /6/ ስር የሚወድቅ መሆኑን ያጣራል። ሁለተኛ ምክንያቱ በድንጋጌው ስር የሚሸፈን እውነት ስለመሆኑ ከማስረጃ ረገድ ይፈትሻል። ሁለቱን በማጣመር ምርምራ ካደረገ በኋላ የሚደርስበት ውሳኔ ጥያቄውን መቀበልና ማጽደቅ ወይም ውድቅ ማድረግ ሊሆን ይችላል። ውድቅ በማድረግ የተሰጠ ውሳኔ ሳይከበር ቀርቶ እገዳው ከቀጠለ ህገ-ወጥ ይሆናል። በይግባኝ ካልተቀየረ በስተቀር ውሳኔውን ወደጎን በማድረግ ማገድ ህጉን ወደ ጎን በማድረግ የተወሰደ ህገ-ወጥ እገዳ ይሆናል። ሚኒስቴሩ ወይም አግባብ ያለው ባለስልጣን በቂ ምክንያት መኖሩን በማረጋገጥ ጥያቄውን ቢያፀድቀውም ከሚወስነው የእገዳ ጊዜ ወይም በህግ ከተቀመጠው የዘጠና ቀናት ከፍተኛ የእገዳ ጊዜ ካለፈ አሁንም እገዳው ህጋዊነት ይጎድለዋል።

ከላይ በተመለከቱት ሁለት ሁኔታዎች እገዳ ህገ-ወጥ መሆኑ ከተረጋገጠ በውጤት ደረጃ የሥራ ውል እንዳልታገደ ይቆጠራል። ይህም ማለት የታገደው ሠራተኛ ለእገዳው ጊዜ ደመወዙ ተከፍሎት ወደ ሥራው ይመለሳል። ከዚህ በተጨማሪ አሠሪው የሚወስደው ህገ-ወጥ የማገድ እርምጃ በሥራ ውሉ እና በአሠሪና ሠራተኛ ህጉ የተጣለበትን ሥራ የመስጠት እና ደመወዝ የመክፈል ዋነኛ ግዴታ መጣስ እንደመሆኑ ለዚህ ተግባሩ ካሳ ከመክፈል አይድንም። የካሳው አወሳሰን በአሠሪና ሠራተኛ ህጉ ላይ ባይኖርም ጉዳዩ የቀረበለት የሥራ ክርክር ሰሚ አካል የውል ህግ ጠቅላላ ደንቦችን ተፈጻሚ በማድረግ ካሳ መወሰን ይችላል። የውል ህግ ጠቅላላ ደንቦች የሥራ ውልን ጨምሮ በሁሉም ውሎች ተፈጻሚ እንደመሆናቸው በልዩ ውል ባልተሸፈነ ጉዳይ ጠቅላላው ደንብ ተፈጻሚ ይሆናል።


[1] አዋጅ ቁ. 1156/2011 አንቀጽ 22

[2] አዋጅ ቁ. 1156/2011 አንቀጽ 19

አሠሪና ሠራተኛ ህግ ንድፈ—ሀሳባዊ ምልከታዎች

አሠሪና ሠራተኛ ህግ ንድፈ—ሀሳባዊ ምልከታዎች

በአሠሪና ሠራተኛ ህግ እድገት ታሪካዊ ሂደት ውስጥ ኢኮኖሚክስንና ሰብዓዊ መብትን መሠረት ያደረጉ ሁለት ግዙፍ የአስተሳሰብ አቅጣጫዎች በተለያየ ደረጃ አሻራቸውን አሳርፈዋል። ኢኮኖሚክስን መነሻ በማድረግ የተቃኙ አስተሳሰቦች የአሠሪና ሠራተኛ ህግን የሚያዩበትና የሚመዝኑበት መነጽር ምርታማነትንና የነጻ ገበያ ውድድርን ማዕከል ያደርጋል። የዚህ አስተሳሰብ ቀንደኛ አራማጆች ከሆኑት መካከል ኒዮክላሲካል ኢኮኖሚስቶች (neoclassical economists) አነስተኛ የሥራ ሁኔታዎችን የሚያዩት እንደ ጫና (ሸክም) ነው። ለምሳሌ ሠራተኛው እረፍት ሲወጣ አሠሪው ስራ ለማይሰራ ሠራተኛ ደመወዝ እንዲከፍል ይገደዳል። እረፍት በወጡ ሠራተኞች ምክንያት ትርፍና ምርታማነት እንዳይቀንስ አሠሪው የሚኖረው አማራጭ በስራ ገበታ ያሉትን ሠራተኞች ስራውን ደርበው እንዲሰሩ ማድረግ ወይም አዲስ ምትክ ሠራተኞችን ቀጥሮ ማሰራት ነው። የመጀመሪያው አማራጭ ምርታማነትን ይቀንሳል። ሁለተኛው ደግሞ ለተጨማሪ ወጪ ይዳርጋል።

በሁለተኛው አማራጭ አሠሪው ለምትክ ሠራተኞች በሚከፍለው ደመወዝ የተነሳ ለተጨማሪ ወጪ ስለሚዳረግ በሚያመርተው ምርት ወይም በሚሰጠው አገልግሎት ላይ የዋጋ ጭማሪ ለማድረግ ይገደዳል። ዋጋ በጨመረ ቁጥር በገበያ ተወዳዳሪ ሆኖ ለመውጣት ያቅተዋል። ስለሆነም በኒዮክላሲካል ኢኮኖሚስቶች አመለካከት በመንግስት የሚደነገጉ አነስተኛ የስራ ሁኔታዎች በምርታማነት ላይ ደንቃራ እንቅፋት በመፍጠር ጤናማ የገበያ ውድድርን ስለሚያዳክሙ በኢኮኖሚ ዕድገት ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ ያስከትላሉ። በዚህም የተነሳ እነዚህ ኢኮኖሚስቶች የዓመት ፈቃድን ጨምሮ ሌሎች የስራ ሁኔታዎች አስገዳጅ በሆነ መልኩ በህግ መደንገግ እንደሌለባቸው ይሟገታሉ።

ከእነዚህ ኢኮኖሚስቶች ጎራ የወጡትና ኒው ኢንስቲቱሸናሊስት (new institutionalist) በመባል የሚጠሩት ደግሞ በመነሻው ባይሆንም በመድረሻው ላይ የተለያ አመለካከት አላቸው። ሀሳባቸው ሲጠቃለል አነስተኛ የሠራተኛ መብቶች ምርታማነትን ከማሳደግ አንጻር አሠሪውን ተጠቃሚ ያደርጉታል የሚል ነው። ስለሆነም በስራ ሰዓት ላይ የሚደረግ ገደብ ምርታማነትን የሚቀንስ ሳይሆን በተቃራኒው ስለሚጨምር ከዚህ አንጻር ተቀባይነት ሊኖረው ይገባል። ለምሳሌ ለቁፋሮ የተቀጠረ ሠራተኛ በተከታታይ ያለ ዕረፍት ለአስራ ስድስት ሰዓታት ከሚቆፍር ይልቅ በቀን ስምንት ሰዓት ቢቆፍር በስራው የበለጠ ውጤት ያስገኛል። በቀን፣ በሳምንትና በዓመት የተወሰነ ዕረፍት ቢሰጠው ደግሞ የበለጠ ውጤታማ ይሆናል። ኒው ኢንስቲቱሺናሊስቶች በህግ የሚደነገጉ አነስተኛ የሠራተኛ መብቶች አስፈላጊነት ይቀበላሉ። አስፈላጊነታቸውን የሚመዝኑት ግን ከምርታማነት ማለትም ለአሠሪው ከሚያስገኙት ጥቅም አንጻር ነው። ስለሆነም የዓመት ፈቃድ የሚያስፈልግበት ምክንያት ሠራተኛው አካሉ እና አዕምሮው ታድሶ በብቃት ለመስራት እንዲያስችለውና በዚህም ውጤታማነቱ እንዲጨምር ነው።

ከላይኞቹ አስተሳሰቦች በተቃራኒ የሚገኘው ሰብዓዊ መብትን ማዕከል ያደረገ አቀራረብ መነሻውም ሆነ መድረሻው ሠራተኛው ነው። በዚህ መሠረት ለሠራተኞች መብቶች በህግ ዕውቅና መስጠት የሚያስፈልግበት ዋና ምክንያት ሠራተኛው ሰብዓዊ ክብሩ እና ጤንነቱ በአሠሪው እንዳይጣስ ከለላ ለመስጠት ነው። አነስተኛ የሥራ ሁኔታዎች የአሠሪውን ምርታማነት አሳደጉም አላሳደጉም ለሠራተኛው በህግ ሊታወቁለት ይገባል። ሠራተኛው በቀን አስራ ስድስት ሰዓት መስራት የማይኖርበት በስራው ውጤታማ ስለማይሆን አይደለም። ይልቅስ አስራ ስድስት ሰዓት ማሰራት ኢ-ሰብዓዊ የጉልበት ብዝበዛ በመሆኑ ነው። በቀን፣ በሳምንት፣ በዓመት ዕረፍት ያስፈለገበት መሰረታዊ ምክንያት የበለጠ ለስራው ብቁ ስለሚያደርገው በዚህም የአሠሪው ምርታማነት እንዲጨምር አይደለም። ከዚያ ይልቅ መሰረታዊ ምክንያቱ ካለዕረፍት ማሰራት የሠራተኛን ሰብዓዊ ክብር የሚንድ ተግባር በመሆኑ ብቻ ነው። ስለሆነም በዚህ በሁለተኛው የአስተሳሰብ መስመር አስገዳጅነት ያላቸውን አነስተኛ ሁኔታዎች በመወሰን ከአሠሪ ኢ-ፍትሃዊ ድርጊቶች ከለላ እና ጥበቃ የሚያደርግ ህግ ሊኖር ይገባል።

አሠሪና ሠራተኛ ህግ እና የፍትሐ ብሔር ስነ-ስርዓት ህግ

የስነ-ስርዓት ህግ ግብ በፍርድ ቤት የሚካሄዱ ክርክሮች ቀልጣፋ፤ ወጪ ቆጣቢና ፍትሐዊ በሆነ መንገድ እንዲቋጩ ማስቻል ነው።  የዚህ ግብ መሳካት በተለይ በሥራ ክርክሮች ላይ የተለየ እንደምታ አለው። የሥራ ውል መቋረጥ በሠራተኛው እና በቤተሰቡ ዕለታዊ ኑሮ ላይ ከሚያሳድረው ከባድ ጫና አንጻር አሠሪው ላይ የሚያቀርባቸው የመብት ጥያቄዎች ሳይውሉ ሳያድሩ በፍጥነት መቋጨት ይኖርባቸዋል። ይህን እውን ለማድረግ የአሠሪና ሠራተኛ አዋጁ ከፊል የስነ-ስርዓት ድንጋጌዎች የሥራ ክርክርን ልዩ ባህርያት ግምት ባስገባ መልኩ እንዲቀረጹ ተደርጓል።

በሁለቱም ወገን ለአሠሪና ሠራተኛ ወሳኝ ቦርድ የሚቀርብ እንዲሁም በሠራተኛ ወይም በሠራተኛ ማህበር ለፍርድ ቤት የሚቀርብ የሥራ ክርክር ከዳኝነት ክፍያ ነፃ መሆኑ[1]፤ ቦርዱ የቀረበለትን ጉዳይ በ30 ቀናት[2]ይግባኝ ሰሚ ሥራ ክርክር ችሎት ደግሞ በ60 ቀናት ውስጥ ውሳኔ መስጠት ያለባቸው መሆኑ[3]፤ አማራጭ የሥራ ክርክር መፍቻ ዘዴዎች በህጉ መዘርጋታቸው[4] እንዲሁም የቋሚ ወይም ጊዜያዊ አሠሪና ሠራተኛ ወሳኝ ቦርድ በልዩ የስነ-ስርዓት ደንቦች እንዲገዛ መደረጉ[5] እና ቦርዱ የራሱን ስነ-ስርዓት ደንቦች እንዲያወጣ ስልጣን መሰጠቱ[6]ሁሉም የሥራ ክርክሮችን የተለየ ባህርይ ግምት ውስጥ በማስገባት የተቀረጹ የስነ-ስርዓት ድንጋጌዎች ናቸው። በአጠቃላይ አነጋገር ለአሠሪና ሠራተኛ ህግ መሰረታዊ ዓላማዎች ውጤታማ ስኬት በልኩ የተሰፋ የስነ-ስርዓት ህግ እንደሚያስፈልግ ግንዛቤ ሊወሰድበት ይገባል።

አሠሪና ሠራተኛ ህጉ ላይ ያሉ ልዩ የስነ-ስርዓት ደንቦች ለህጉ ውጤታማ አተገባበር ምን ያህል በቂ ናቸው? በተጨባጭ ያመጡት ለውጥስ እንዴት ይመዘናል? የሚለው ጥያቄ ራሱን የቻለ ዳሰሳ ይፈልጋል። በዚህ የተነሳ ዝምድናቸውን በተለይም በሥራ ክርክር ወቅት የስነ-ስርዓቱ ድንጋጌዎች የአሠሪና ሠራተኛ ህጉን ዓላማ ውጤት በሚሰጥ መልኩ የመተርጎም አስፈላጊነት ለማሳየት ያክል ‘በፍርድ ያለቀ ጉዳይ’ ተፈጻሚ የሆነበት መንገድ እንደሚከተለው ተዳሷል። 

በፍርድ ያለቀ ጉዳይ

በሥራ ክርክር ችሎት ሠራተኛው የፈፀመው ድርጊት ከሥራ ለማሰናበት በቂ አይደለም ተብሎ መወሰኑ አሠሪው በሠራተኛው ላይ በፍትሐብሔር ጉዳይ ሊያቀርብ የሚችለውን ክስ የሚያስቀር የመጨረሻ ፍርድ /ውሳኔ/ አይደለም። (አመልካች የኢትዮጵያ እህሌ ንግድ ድርጅት እና ተጠሪ እነ ኃይለየሱስ ቱኪ /4 ሰዎች/ ሰ/መ/ቁ. 44588 ቅጽ 10 ሚያዝያ 4 ቀን 2002 ዓ.ም) በዚህ ነጥብ ችሎቱ እንዳብራራው፤

የአሠሪና ሠራተኛ ክርክር ችሎት የሚወሰነው መሰረታዊ ጭብጥ ሠራተኛው በፍትሐብሔር ተጠያቂነትና ኃላፊነት አለበት ወይስ የለበትም? የሚለው ሣይሆን አሠሪው ሠራተኛውን ከሥራ ለማሰናበት የሚያበቃ በቂ ምክንያት አለ ወይስ የለም? የሥራ ስንብቱ የሕጉን ሥርአት ተከትሎ የተፈፀመ ነው ወይስ አይደለም? የሚለው ነው።

የችሎቱ አነጋገር ከፊል እውነት ቢኖረውም መነሻው ድርጊት በፍትሐብሔር ሆነ በአሠሪና ሠራተኛ ህግ ተመሳሳይ የሚሆንበት አጋጣሚ ሰፊ እንደሆነ መዘንጋት የለበትም። በእንደዚህ ዓይነት ሁኔታዎች ሠራተኛው በአንደኛው ህግ ከሀላፊነት ነጻ በሌላኛው ህግ ደግሞ ሀላፊ የሚሆንበት የህግ መሰረት የለም። ‘ገንዘብ አጉድለሀል’ በሚል ከሥራ የተሰናበተ ሠራተኛ አለማጉደሉ ተረጋግጦ ስንብቱ ህገ-ወጥ ከተደረገ በፍትሐብሔር ለጉደለቱ ተጠያቂ ሆኖ እንዲከፍል ሊወሰንበት አይገባም። እንዲህ ዓይነት ድምዳሜ ላይ መድረስ የአሠሪና ሠራተኛ ህግ ሙሉ በሙሉ ከፍትሐብሔር ህግ ተነጥሎ ራሱ የቻለ የህግ ክፍል እንደሆነ ያልተገባ አቋም እንደመያዝ ይቆጠራል። በሁለቱ መካከል ልዩነት መኖሩ ባይካድም የልዩነታቸው መልክ እንደ ወንጀል እና ፍትሐብሔር ህግ ጫፍ እና ጫፍ የሚያራርቃቸው አይደለም።

ፍርድ ያገኘው ጉዳይ እና አዲስ የሚጠየቀው ዳኝነት ሁለቱም የሥራ ክርክሮች በሚሆኑበት ጊዜ በመርህ ደረጃ የፍ/ስ/ስህ/ቁ. 5 ያለቅደመ ሁኔታ ተፈጻሚነት ሊያገኝ የሚገባ ቢሆንም ይህ አነጋገር ግን በጊዜ ሂደት ድጋሚ መሆናቸው ቀርቶ አዲስ መልክ የሚይዙ የመብት ጥያቄዎችን አያጠቃልልም። ክሱ በቀረበበት ወቅት የማይኖር መብት ከጊዜ በኋላ ሊፈጠር ስለሚችል ጥያቄው ‘በፍርድ ያለቀ’ ተብሎ ውድቅ ሊደረግ አይገባም።

ይህ መሰረታዊ ሀሳብ በሰ/መ/ቁ 12380 (አመልካች የግብርና ምርት ማሣደጊያዎች አቅራቢ ድርጅት እና ተጠሪ አቶ ጀማል አሕመድ ጥቅምት 16 ቀን 1999 ዓ.ም. ያልታተመ) ላይ በጥንቃቄ ባለመፈተሹ የስነ ስርዓት ህጉ በተዛባ መንገድ እንዲተረጎም ምክንያት ሆኗል። በዚህ መዝገብ ተጠሪ በአመልካች ድርጅት ውስጥ በጫኝና አውራጅነት ሥራ ብር 1000 (አንድ ሺ ብር) እየተከፈላቸው ከ1974 ዓ.ም. ጀምሮ እስከ መስከረም 1994 ዓ.ም. ድረስ ሲሰሩ ቆይተው የሥራ ውላቸው ከህግ ውጭ በመቋረጡ ካሳ፣ የስንብት ክፍያ፣ የ17 ዓመት የበዓላት ክፍያ እና የዓመት እረፍት ክፍያ እንዲከፈላቸው በስር ፍ/ቤት ተወስኖላቸዋል። አመልካች በበኩሉ ውሳኔው በሰበር ችሎት እንዲታረምለት አቤቱታውን አቅርቧል። በተጨማሪም የአሁን ተጠሪ ቀደም ሲል ከሌሎች ሠራተኞች ጋር በመሆን የቋሚነት ጥያቄ አቅርበው ውድቅ መደረጉን የሚያሳይ የውሳኔ ግልባጭ ከአቤቱታው ጋር አያይዟል።

በሰበር ውሳኔው ላይ እንደተዘገበው አመልካች ቅሬታ ያደረበት ተጠሪ ቋሚ ሠራተኛ ተብለው ከ1974 ዓ.ም. እስከ 1994 ዓ.ም. ድረስ ያለው የበዓላት ክፍያ እና የዓመት እረፍት እንዲከፈላቸው በስር ፍ/ቤት በተሰጠው የውሳኔ ክፍል ላይ ነው። ሆኖም የቋሚነት ጥያቄውን አስመልክቶ አመልካች በስር ፍ/ቤት የመጀመሪያ ደረጃ መቃወሚያ አላነሳም። በተጨማሪም የታለፈበት ወይም ውድቅ የተደረገበት መቃወሚያ ስለመኖሩ በመጥቀስ አልተከራከረም።

ከተረጋገጡት ፍሬ ነገሮችና ከአመልካች ክርክር ብሎም ከስር ፍ/ቤት ውሳኔ ይዘት አንጻር የሥራ ውሉ የቆይታ ጊዜ እና የመቋረጡ ህጋዊነት በጭብጥነት ተይዘው መመርመር ያለባቸው መሰረታዊ ጉዳዮች ናቸው። ከዚህ በተቃራኒ ችሎቱ የመሰረተው ጭብጥ “የአሁኑ ተጠሪ ክርክር በፍ/ሥ/ሥ/ህ/ቁ. 5 መሰረት ተቀባይነት ሊኖረው ይገባል ወይስ አይገባም?” የሚል ነው። የተሳሳተ ጭብጥ ወደ ተሳሳተ ውሳኔ እንደሚያመራ ግልጽ ነው። ይህ እንደተጠበቀ ሆኖ ችሎቱ የስር ፍ/ቤትን ውሳኔ ሲሽር ከጭብጥ አያያዝ የማይመዘዙ ተጨማሪ ስህተቶችን ሰርቷል።

ከላይ ለማመልከት እንደተሞከረው ተጠሪ ለሰበር ክርክሩ መነሻ ከሆነው ክስ በፊት ከሌሎች ሠራተኞች ጋር በመሆን የቋሚነት ጥያቄ አቅርበው የነበረ ቢሆንም ተቀባይነት አላገኘም። ተቀባይነት አለማግኘቱ የስር ፍ/ቤትን ውሳኔ ለመሻር በችሎቱ ዘንድ በቂና ብቸኛ ምክንያት ተደርጎ ተወስዷል። በዚህ ነጥብ ላይ ሐተታው እንደሚከተለው ይነበባል።

…ተጠሪ በጉዳዩ ላይ ቀደም ሲል ሥልጣን ባለው አካል ውሳኔ እንዳልተሰጠ በማስመሰል…በድጋሚ አዲስ ክስ በማቅረብ ተወስኖ እንዲፀና የተደረገው ውሳኔ በፍ/ሥ/ሥ/ህ/ቁ. 5 የሚቃረን መሠረታዊ የህግ ሥህተት ነው ብለናል።

ድምዳሜው በአንክሮ ሲፈተሽ ግድፈቶቹ ጎልተው ይታያሉ። ለመጥቀስ ያክል፤

  • መቃወሚያው በስር ፍ/ቤት አልተነሳም። ውሳኔም አላረፈበትም። የፍ/ሥ/ሥ/ህ/ቁ. 5 በመቃወሚያነት በስር ፍ/ቤት ሳይነሳ በሰበር የሚስተናገድበት ስርዓት የለም። የፍትሐ ብሔር ስነ ስርዓት ህጉም በግልጽ ይከለክላል።[7] የሰበር ችሎት ስልጣን መሰረታዊ የህግ ስህተት ያለበትን ውሳኔ ማረም እንጂ በመቃወሚያ ላይ ብይን መስጠት አይደለም። ከፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 5 ጋር በተያያዘ የስር ፍ/ቤቶች የሰጡት ብይን ሆነ ውሳኔ የለም። ውሳኔ ያላረፈበት ጉዳይ ከችሎቱ የስልጣን ክልል ውጪ ነው። ጉዳዩ ውሳኔ ስላላረፈበት በሐተታው የተተቸው የስር ፍ/ቤት ሳይሆን ተጠሪ ነው። “ተጠሪ በጉዳዩ ላይ ቀደም ሲል ሥልጣን ባለው አካል ውሳኔ እንዳልተሰጠ በማስመሰል…” የሚለው አገላለጽ በእርግጥ የታረመው የተጠሪ ስህተት ነው ወይስ የስር ፍ/ቤቶች? ብለን እንድንጠይቅ ያስገድደናል።
  • ተጠሪ ቀድሞ ክስ ያቀረቡበት ጉዳይ እና በሰ/መ/ቁ 12380 በስር ፍ/ቤት ዳኝነት የጠየቁበት ጉዳይ ለየቅል ናቸው። የቋሚ ልሁን ጥያቄ ከሥራ ውል መቋረጥ ብሎም ከበዓላትና የዓመት እረፍት የክፍያ ጥያቄ ጋር ምን ያገናኘዋል? የሥረ ነገርና የጭብጥ አንድነት በሌለበት የፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 5 ድንጋጌ እንደ መቃወሚያ ተነስቶ መዝገብ አያዘጋም። የስር ፍ/ቤትን ውሳኔ አያስለውጥም።
  • የተጠሪ የቋሚነት ጥያቄ አስቀድሞ በፍርድ የተወሰነ ነው ቢባል እንኳን በውጤት ደረጃ የስር ፍ/ቤትን ውሳኔ ሙሉ በሙሉ ለመሻር የሚያስችል በቂ ምክንያት አይደለም። ሊሻር የሚችለው ቋሚነትን አስመልክቶ በስር ፍ/ቤት የተሰጠው የውሳኔ ክፍል ብቻ ነው። የመሻሩ ውጤት ተጠሪ ለተወሰነ ሥራ ወይም ጊዜ መቀጠራቸውን ድምዳሜ ላይ ከሚያደርስ በስተቀር የሥራ ውሉን መቋረጥ ህጋዊ አያደርገውም። የውሉ መቋረጥ ህጋዊነት ከአዋጁ አንቀጽ 24(4) አንጻር በጭብጥነት ተይዞ ሊመረመር ይገባው ነበር።

ችሎቱ የፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ 5 ድንጋጌን ቀጣይነት እና ዘላቂነት ባለው የቅጥር ግንኙነት ላይ ሁልጊዜ ተፈጻሚ ማድረጉ አግባብነት እንደሌለው በጊዜ ሂደት የተረዳው ይመስላል። ከአራት ዓመታት በኋላ በሰ/መ/ቁ 66242 (አመልካች ሙሉ ደምሴ እና ተጠሪ ሸራተን አዲስ ሐምሌ 13 ቀን 2003 ዓ.ም. ቅጽ 9) የተንጸባረቀው አቋም የሰ/መ/ቁ 12380 የህግ ትርጉም በግልጽ መለወጡን ባይጠቅስም በውጤት ደረጃ የአስገዳጅነት ኃይሉን እንዳሳጣው በእርግጠኝነት መናገር ይችላል። በሰ/መ/ቁ 66241 አመልካች ካቀረቡት የተለያዩ የክፍያ ጥያቄዎች መካከል ከፊሉ ቀደም ሲል በፍ/ቤት ውሳኔ ውድቅ ተደርጎባቸዋል። አመልካች ውሳኔ ባገኘው ጉዳይ ላይ በድጋሚ ክስ ሲመሰርቱ የስር ፍ/ቤቶች ጉዳዩ አስቀድሞ ውሳኔ እንዳገኘ በመጠቆም የፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ 5 ድንጋጌን ጠቅሰው ሳይቀበሉት ቀርተዋል። ይሁን እንጂ የስር ፍ/ቤቶች የስነ ስርዓት ህጉን ድንጋጌ ከቅጥር ግንኙነት ልዩ ባህርይ አንጻር ማጣጣም ባለመቻላቸው በዚህ ነጥብ ላይ የሰጡት ውሳኔ መሰረታዊ የህግ ስህተት ተፈጽሞበታል በሚል ተሽሯል። የተጣጣመው የችሎቱ የህግ ትርጉም እንደሚከተለው ይነበባል።

የአሠሪና ሠራተኛ ግንኙነት ካለው ቀጣይነትና ዘላቂነት አንጻር…ሠራተኛው በአንድ ወቅት ሊጠበቅልኝ ወይም ሊከፈለኝ ይገባል በማለት ያቀረበው የመብት ወይም የክፍያ ጥያቄ በፍርድ ቤት ውድቅ መደረጉ በሌላ ጊዜ መብቱን ወይም ክፍያውን ለመጠየቅ የሚያስችለውን የስራ ውል የህግ ድንጋጌ ወይም የህብረት ስምምነት ዋቢ በማድረግ እንዳይጠይቅ የሚገድበው አይደለም።


[1] አዋጅ ቁ. 1156/2011 አንቀጽ 162

[2] አዋጅ ቁ. 1156/2011 አንቀጽ 152/1/

[3] አዋጅ ቁ. 1156/2011

[4] አዋጅ ቁ. 1156/2011 አንቀጽ 141-144

[5] አዋጅ ቁ. 1156/2011 አንቀጽ 147

[6] አዋጅ ቁ. 1156/2011 አንቀጽ 149

[7] ፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 244(3) ይመለከቷል፡፡

የቅጥር ግንኙነት

የአሠሪና ሠራተኛ ሕግ መነሻውና ምንጩ በቅጥር ላይ የተመሰረተ ግንኙነት ሲሆን ይህም በአንድ ተቀጣሪ ሠራተኛ እና ቀጣሪ ግለሰብ ወይም ድርጅት መካከል ይፈጠራል። የግንኙነቱ ደረጃ በአንድ ግለሰብ ሠራተኛ እና አሠሪ መካከል ሲወሰን ‘የግል የቅጥር ግንኙነት’ (Individual Employment Relationship) በመባል ሲታወቅ በአሠሪ እና በሠራተኛ ማህበር ወይም ማህበራት መካከል ሲፈጠር ደግሞ ‘የወል የሥራ ግንኙነት’ (Collective Employment Relationship) እየተባለ ይጠራል።

ልውውጥ እና የመደራደር አቅም ግላዊ የሆነው የቅጥር ግንኙነት ዋነኛ መገለጫ ባህርያት ናቸው። በልውውጥ ግንኙነት (Exchange Relationship) ሠራተኛው ለሚያበረክተው አገልግሎት ክፍያ ይሰጠዋል። አሠሪው ደግሞ ለሚከፈለው ክፍያ አገልግሎት ያገኛል።[1] እንዲህ ዓይነቱ የ‘ሰጥቶ መቀበል’ ግንኙነት መኖር ግላዊ የቅጥር ግንኙነት መሰረቱ በተዋዋይ ወገኖች ፈቃድ ላይ ተተክሎ እንደቆመ ያሳየናል። ሠራተኛውንና አሠሪውን ያስተሳሰራቸው ገመድ ይኸው ወደውና ፈቅደው የሥራ ግንኙነት ለመመስረት የሚያደርጉት ስምምነት ነው።

የቅጥር ግንኙነት መነሻው የተዋዋይ ወገኖች ፈቃድ በመሆኑ ይዘቱ በአንደኛው ወገን የተናጠል እርምጃ አይቀየርም። አይለወጥም። የፈቃድ መኖር ሌላም እንደምታ አለው። ይኸውም ይህን ባህርይ የማይጋሩ ግንኙነቶች ከአሠሪና ሠራተኛ ህግ ወሰን ውጪ እንዲሆኑ ያደርጋል። ስለሆነም ‘ተገዶ መስራት’ (Compulsory Labour) የግንኙነቱ መነሻ ከፈቃድ ይልቅ ግዴታ በመሆኑ በአሠሪና ሠራተኛ ህግ አይገዛም። በታራሚዎች የሚሠራ ሥራ ለዚህ ጥሩ ምሳሌ ሊሆነን ይችላል። ከተወሰኑ ታራሚዎች በስተቀር በፌደራል ሆነ በክልል ማረሚያ ቤቶች ውስጥ የሚገኙ ታራሚዎች እንደየሥራ ችሎታቸው፣ ሙያቸውና ጠባያቸው ሥራ መስራት ያለባቸው ሲሆን ለሚሰሩት ሥራም የተወሰነ ክፍያ ይከፈላቸዋል።[2] ታራሚዎች ሥራ ሰርተው ክፍያ ቢከፈላቸውም ከሚያሰራቸው ማረሚያ ቤት ጋር ያላቸው የሥራ ግንኙነት በግዴታ ላይ በመመስረቱ በሁለቱ መካከል በቅጥር ላይ የተመሰረተ የሥራ ግንኙነት አይፈጠርም። የአሠሪና ሠራተኛ ህጉም ተፈጻሚ አይሆንም።

የፈቃድ መኖር አስፈላጊ ቅድመ ሁኔታ ቢሆንም ልውውጥ በሌለበት ብቻውን ግንኙነቱን እንደማይመሰርት ልብ ሊባል ይገባል። ለምሳሌ በጎ ፈቃደኞች እንደ ማንኛውም ሠራተኛ በተለያየ መስክ ተሰማርተው ሥራ ይሰራሉ። ሆኖም ለሚሰሩት ሥራ ደመወዝ ስለማይከፈላቸው ከሚያሰራቸው አካል ጋር ያላቸው ግንኙነት በቅጥር ግንኙነት ውስጥ አይወድቅም። በተመሳሳይ መልኩ በአሠሪው ተቀጥሮ ሲሰራ የነበረ ሠራተኛ ሲሞት አሠሪው በራሱ ፈቃድና ፍላጎት በሟች ሲረዱ ለነበሩ ጥገኞች ደመወዝ መክፈሉን ቢቀጥል በሁለቱ መካከል የሥራ ግንኙነት አይመሰረትም።

ግላዊ የቅጥር ግንኙነት በመርህ ደረጃ በውዴታና በፈቃድ ቢመሰረትም ተዋዋይ ወገኖች የግንኙነታቸውን ይዘት ለመወሰን ያላቸው ነጻነት ወይም የመደራደር አቅም ሰፊ ልዩነት ይታይበታል። በሥራ ገበያ ላይ ያለው የገዘፈ የአቅርቦትና ፍላጎት ልዩነት ሠራተኛውን ‘ፈላጊ’ አሠሪውን ደግሞ ‘ተፈላጊ’ አድርጎታል። ቅጥር ለሠራተኛው ዕድል ለአሠሪው ደግሞ ፍላጎት ነው። ሠራተኛው ለመቀጠር ሲፈልግ አይደለም የሚቀጠረው፤ የሥራ ዕድል ሲያገኝ እንጂ። አሠሪው ደግሞ ሠራተኛ መቅጠር ሲፈልግ ይቀጥራል። የመቅጠር ፍላጎት እንጂ ዕድል አያስፈልገውም።

የአሠሪው ኢኮኖሚያዊ የበላይነት የግንኙነቱን ዝርዝር ይዘት ብቻውን በተናጠል እንዲወስን የተመቻቸ ሁኔታ ይፈጥርለታል። ሠራተኛው በአንጻሩ አሠሪው መጥኖ የሰጠውን መብት ብቻ ለመቀበል ይገደዳል። ይህን መሰሉ የበታችና የበላይ ግንኙነት ለሁለቱ ወገኖች ብቻ ከተተወ የአሠሪና ሠራተኛ ግንኙነት መሆኑ ቀርቶ የጌታና ሎሌ ይሆናል። ይህ ደግሞ አስከፊ የጉልበት ብዝበዛና የመብት ረገጣ ማስከተሉ አይቀሬ ነው። የመደራደር አቅም ልዩነት መኖር መንግስት በግንኙነቱ ውስጥ ጣልቃ ገብቶ ግንኙነቱን እንዲቆጣጠረው አስገዳጅ ምክንያት ሆኗል። የመንግስት ሚና በዋነኛነት በስምምነት የማይቀየሩ አነስተኛ የሥራ ሁኔታዎችንና ደረጃዎችን በህግ መወሰን ነው።


[1] Brian Willey, Employment Law in Context: An Introduction for HR Professionals. (2nd edn, Harlow: Pearson Education Limited, 2003) ገጽ 48

[2] ስለፌደራል ታራሚዎች አያያዝ የወጣ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁ. 138/1999 አንቀጽ 30-32 እንዲሁም በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት የህግ ታራሚዎች አያያዝና አጠባበቅ መወሰኛ ክልል መስተዳደር ምክር ቤት ደንብ ቁ. 26/1997 አንቀጽ 19-21

አዋጅ ቁጥር ፮፻፱/፪ሺ፩ ዓ.ም የተጨማሪ እሴት ታክስ /ማሻሻያ/ አዋጅ

                   አዋጅ ቁጥር ፮፻፱/፪ሺ፩ ዓ.ም.

የተጨማሪ እሴት ታክስ /ማሻሻያ/ አዋጅ

የተጨማሪ እሴት ታክስ አዋጅ ቁጥር ፪፻፹፭/፲፱፻፺፬፺ ማሻሻል አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ፣
በኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ ሕገ መንግሥት አንቀጽ ፶፭ ንዑስ አንቀፅ /፩/ እና /፲፩/ መሠረት የሚከተለው ታውጇል፡፡

. አጭርርዕስ
ይህ አዋጅ ‹‹የተጨማሪ እሴት ታክስ /ማሻሻያ/ አዋጅ ቁጥር ፮፻፱/፪ሺ፩›› ተብሎ ሊጠቀስ ይችላል፡፡

. ማሻሻያ
የተጨማሪ እሴት ታክስ አዋጅ ቁጥር ፪፻፹፭/፲፱፻፺፬ እንደሚከተለው ተሻሽሏል፣
፩/ የአዋጁ አንቀጽ ፪ ንዑስ አንቀጽ /፬/ ተሰርዞ በሚከተለው አዲስ ንዑስ አንቀጽ /፬/ ተተክቷል፣
‹‹፬/ ‹‹ባለሥልጣን›› ማለት የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ነው፤››
፪/ ከአዋጁ አንቀጽ ፪ ሥር የሚከተሉት አዲስ ንዑስ አንቀጽ /፳፭/ እና /፳፮/ ተጨምረዋል፡፡
‹‹፳፭/ ‹‹የሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያ›› ማለት የጥሬ ገንዘብ መመዝገቢያ መሣሪያ ወይም የሽያጭ ነቁጣ መሣሪያ ነው፣
‹‹፳፮/ ‹‹አቅራቢ›› ማለት የሽያል መመዝገቢያ መሣሪያዎችን ወይም በመሣሪያው ላይ ተጭኖ አገልግሎት የሚሰጥ ሶፍት ዌርን ወይም ሁለቱንም በአንድ ላይ የሚያቀርብ ሰው ነው፡፡››
፫/ በአዋጁ አንቀጽ ፮ ውስጥ ‹‹በማንኛውም ሰው›› የሚለው ሐረግ ተሰርዞ ‹በማንኛውም የተመዘገበ ሰው›› እንደዚሁም ‹‹ባለማቋረጥ ወይም በመደበኛ ሥራነት›› የሚለው ሐረግ ተሰርዞ ‹‹በመደበኛም ሆነ መደበኛ ባልሆነ መንገድ›› በሚለው ተተክቷል፡፡
፬/ ከአዋጁ አንቀጽ ፯ ንዑስ አንቀጽ /፬/ ቀጥሎ የሚከተለው አዲስ ንዑስ አንቀጽ /፭/ ተጨምሯል፣
‹‹፭/ የዚህ አንቀጽ ንዑስ አንቀጽ ፩/ሀ/ ተፈፃሚ የሚሆንበት ግብይት ሲከናወን እንደአስፈላጊነቱ በገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር በሚወጣ መመሪያ መሠረት ታክሱ ግዢውን በሚፈፀመው አካል ተይዞ ለባለሥልጣኑ ይከፈላል፡፡››
፭/ የአዋጁ አንቀጽ ፰ ንዑስ አንቀጽ /፪/ ፊደል ተራ /ሀ/ ተሰርዞ በሚከተለው አዲስ ፊደል ተራ /ሀ/ ተተክቷል፣
‹‹ሀ. ቢያንስ ሁለት ዓመት ያገለገለ የመኖሪያ ቤት ሽያጭና የመኖሪያ ቤት ኪራይ፣››
፮/ በአዋጁ አንቀጽ ፲፩ ንዑስ አንቀጽ /፮/ ውስጥ ‹‹የአንቀጽ ፬ ንዑስ አንቀጽ /፫/ ድንጋጌ›› ተብሎ የተጠቀሰው ተሰርዞ ‹‹የአንቀጽ ፬ ንኡስ አንቀጽ /፪/ ድንጋጌ›› በሚለው ተተክቷል፣
፯/ በአዋጁ አንቀጽ ፲፩ ንዑስ አንቀጽ /፯/ ውስጥ ‹‹የአንቀጽ ፬ ንዑስ አንቀጽ /፬/ ድንጋጌ›› ተብሎ የተጠቀሰው ተሰርዞ ‹‹የአንቀጽ ፬ ንዑስ አንቀጽ /፫/ ድንጋጌ›› በሚለው ተተክቷል፡፡
፰/ በአዋጁ አንቀጽ ፲፩ ንዑስ አንቀጽ /፰/ ውስጥ ‹‹የአንቀጽ ፬ ንዑስ አንቀጽ /፰/ ውስጥ ‹‹የአንቀጽ ፬ ንዑስ አንቀጽ/፭/ ድንጋጌ›› ተብሎ የተጠቀሰው ተሰርዞ ‹‹የአንቀጽ ፬ ንዑስ አንቀጽ /፬/ ድንጋጌ›› በሚለው ተተክቷል፡፡
፱/ የአዋጁ አንቀጽ ፲፮ ንዑስ አንቀጽ /፫/ ተሰርዞ በሚከተለው አዲስ ንዑስ አንቀጽ /፫/ ተተክቷል፡፡
‹‹፫. ለተጨማሪ እሴት ታክስ መመዝገብ ያለበት ሰው በዚህ አንቀጽ ንዑስ አንቀጽ ፩/ሀ/ የተመለከተው ጊዜ ከተጠናቀቀ በኋላ ባለው ወር እስከ መጨረሻ ቀን ወይም በዚህ አንቀጽ ንዑስ አንቀጽ ፩/ለ/ የተመለከተው ጊዜ በተጠናቀቀበት ወር እስከ መጨረሻ ቀን ለምዝገባ ማመልከቻ ማቅረብና መመዝገብ አለበት፡፡››
፲/ በአዋጁ አንቀጽ ፳፪ ንዑስ አንቀጽ /፩/ ተሰርዞ በሚከተለው አዲስ ንዑስ አንቀጽ /፩/ ተተክቷል፣
‹‹፩/ በዚህ አንቀጽ ንዑስ አንቀጽ /፮/ እና /፯/ በሌላ ሁኔታ ካልተወሰነ በስተቀር ለተጨማሪ እሴት ታክስ የተመዘገበና ታክስ የሚከፈልበት ግብይት የሚያካሂድ ሰው ደረሰኝ ወዲያውኑ መስጠት አለበት፡፡ ለተጨማሪ እሴት ታክስ ያልተመዘገበ ሰው የተጨማሪ እሴት ታክስ ደረሰኝ መስጠት አይችልም፡፡››
፲፩/ የአዋጁ አንቀጽ ፳፪ ንዑስ አንቀጽ /፫/ ተሰርዞ ንዑስ አንቀጽ /፬/፣ /፭/፣ /፮/ እና /፯/ እንደ ቅደም ተከተላቸው ንዑስ አንቀጽ /፫/፣ /፬/፣ /፭/ እና /፮/ ሆነዋል፡፡
፲፪/ የአዋጁ አንቀጽ ፳፮ ንዑስ አንቀጽ /፩/ ተሰርዞ በሚከተለው አዲስ ንዑስ አንቀጽ /፩/ ተሰርዞ በሚከተለው አዲስ ንዑስ አንቀጽ /፩/ ተተክቷል፣
‹‹፩/ እያንዳንዱ የተመዘገበ ሰው፣
ሀ/ በአንድ የሂሳብ ጊዜ ውስጥ ታክስ የመክፈል ግዴታ ያለበት ቢሆንም ባይሆንም በእያንዳንዱ የሂሳብ ጊዜ ሂሳቡን ግብር ባለሥልጣኑ ዘንድ በመቅረብ ወይም በኤሌክትሮኒክስ የመገናኛ ዘዴ ወይም ባለሥልጣኑ ለሚወክለው የፋይናንስ ተቋም ማስታወቀ፣ እና
ለ/ ለእያንዳንዱ የሂሳብ ጊዜ የተሰጠውን የመጨረሻ ታክስ መክፈያ ጊዜ ገደብ ጠብቆ ለባለሥልጣኑ ወይም ባለሥልጣኑ ለወከለው ሰው ከገቢ ማስታወቂያው ጋር በአንድነት ታክሱን መክፈል አለበት፡፡››
፲፫/ ከአዋጁ አንቀጽ ፴ ንዑስ አንቀጽ /፪/ ቀጥሎ የሚከተሉት አዲስ ንዑስ አንቀጾች /፫/፣ /፬/ እና /፭/ ተጨምረዋል፣
‹‹፫/ በታክስ ከፋዩ የንግድ ሥራ ቦታ በመገኘት ምርመራ ለማድረግ ሥልጣን የተሰጣቸው የባለሥልጣኑ ሠራተኞች ማናቸውንም ሕገ ወጥ ደረሰኝ ወይም የሂሳብ ሰነድ ወይም የሂሳብ መዝገብ ካገኙ የፍርድ ቤት ትዕዛዝ ሳያስፈልግ ሕገወጥ የሆነውን ደረሰኝ ወይም ሰነድ መያዝ ይችላሉ፡፡ በዚህ ሁኔታ የተያዘ ወይም የተገኘ ሰነድ በማስረጃነት በፍርድ ቤት ዘንድ ተቀባይነት ይኖረዋል፡፡
፬/ ሕገወጥ ደረሰኞችን ወይም ሰነዶችን ለመስጠት ፍቃደኛ ባልሆነ ግብር ከፋይ ላይ የፖሊስ ኃይል በመጠቀም ማስገደድ ይቻላል፡፡
፭/ ለዚህ አንቀጽ ንዑስ አንቀጽ /፫/ አፈፃፀም በባለሥልጣኑ ሠራተኛ ትብብር የተጠየቀ ማናቸውም የፖሊስ ኃይል አባል የመተባበር ግዴታ አለበት፡፡
፲፬/ የአዋጁ አንቀጽ ፵፪ ተሰርዞ በሚከተለው አዲስ አንቀጽ ፵፪ተተክቷል፣

‹‹፵፪/ መቀጫንስለማንሳት
፩/ ባለሥልጣኑ በሚያወጣው መመሪያ መሠረት በታክስ ከፋይ ላይ የተጣለ አስተዳደራዊ መቀጫ በሙሉ ወይም በከፊል እንዲነሳ ለማድረግ ይችላል፡፡
፪/ በዚህ አንቀጽ ንዑስ አንቀጽ /፩/ መሠረት የሚነሳው መቀጫ በዚህ አዋጅ አንቀጽ ፵፯ መሠረት የሚታሰበውን ወለድ አይጨምርም፡፡››
፲፭/ በአዋጁ አንቀጽ ፵፫ ንዑስ አንቀጽ /፪/ ውስጥ ‹‹የሚፈለግበትን ታክስ ካልከፈለ›› ከሚለው ሐረግ ቀጥሎ ‹‹ወይም ይግባኝ ካላቀረበ›› የሚል ሐረግ ተጨምሯል፡፡
፲፮/ የአዋጁ አንቀጽ ፵፭ ንዑስ አንቀጽ /ሀ/፣ /ለ/፣ /ሐ/ እና /መ/ የንዑስ አንቀጽ /፩/ ፊደል ተራ /ሀ/፣ /ለ/፣ /ሐ/ እና /መ/ ሆነው የሚከተለው አዲስ ንዑስ አንቀጽ /፪/ ተጨምሯል፣
‹‹፪/ ለዚህ አንቀጽ ንዑስ አንቀጽ ፩/ለ/ አፈጻጸም ‹‹ሀሰተኛ ደረሰኝ›› ማለት በባለሥልጣኑ ሳይፈቀድ የታተመ ወይም በኮምፒውተር የተዘጋጀ ደረሰኝ ወይም የግዢውን ወይም የሽያጩን ሂሣብ ለማሳነስ ወይም ለመጨመር በማሰብ ወይም በቸልተኛነት በሰነዱ ላይ አሀዝ በመቀነስ ወይም በመጨመር ወይም ተመሳሳይ ቁጥር ያለው ደረሰኝ በማተም ወይም በማባዛት ወይም ሁሉንም ቅጂዎች እንደበራሪ መጠቀም ወይም የሚፈቀደው የታክስ ተቀናሽ ወይም የተመላሽ ሂሣብ እንዲጨምር ወይም የማይገባውን ተመላሽ ለማግኘት ወይም ሌላ ማናቸውም የማጭበርበር ተግባር ለመፈጸም የተዘጋጀ ሰነድ ነው፡፡››
፲፯/ ከአዋጁ አንቀጽ ፵፮ ንዑስ አንቀጽ /፬/ ቀጥሎ የሚከተለው አዲስ ንዑስ አንቀጽ /፭/ ተጨምሯል፣
‹‹፭/ ማናቸውም ታክስ ከፋይ በማንኛውም የሂሳብ ጊዜ ታክስ የሚከፈልበት ግብይት ባይኖረውም የታክስ ማስታወቂያ ካላቀረበ በዚህ አንቀጽ ንዑስ አንጽ ፬/ሀ/ መሠረት ይቀጣል፡፡››
፲፰/ ከአዋጁ አንቀጽ ፵፯ ቀጥሎ የሚከተሉት አዲስ አንቀጽ ፵፯ሀ፣ ፵፯ለ እና ፵፯ሐ ተጨምረዋል፣

‹‹፵፯ሀየሽያጭመመዝገቢያመሣሪያአጠቃቀምግዴታዎችንባለመወጣትየሚጣልመቀጫ
ማንኛውም በሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያ የመጠቀም ግዴታ ያለበት ሰው፣
፩/ ዕውቅና ያልተሰጠው ወይም በባለሥልጣኑ ዘንድ ያልተመዘገበ መሣሪያ ወይም የሽያጭ ነቁጣ ሶፍትዌር ሲጠቀም ከተደረሰበት ለተጠቀመበት ለእያንዳንዱ መሣሪያ ብር ፶ሺ ይቀጣል፣
፪/ መሣሪያው በጥገና ላይ ባለበት ጊዜ ካልሆነ በስተቀር በሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያ ከታተመ ደረሰኝ ውጪ በሌላ ማናቸውም ዓይነት ደረሰኝ ወይም ያለደረሰኝ ግብይት ካከናወነ ብር ፶ሺ ይቀጣል፣
፫/ በሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያ ላይ ጉዳት ያደረሰ ወይም የፊሲካል ማስታወሻው እንዲቀየር ያደረገ ወይም ጉዳት ለማድረስ ወይም ማስታወሻውን ለመቀየር ሙከራ ያደረገ ከሆነ ብር ፩፻ሺ ይቀጣል፣
፬/ የባለሥልጣኑ ሠራተኛ የሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያን ሥርዓት ኦዲት እንዳያደርግ መሰናክል ከፈጠረ ወይም በመሳሪያው ላይ በዓመት አንድ ጊዜ በአገልግሎት ማዕከል የቴክኒክ ምርመራ ካላስደረገ ብር ፳፭ሺ ይቀጣል፣
፭/ በንግድ ሥራው ለሚጠቀምበት የሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያ ከአገልግሎት ማዕከል ጋር ውል ካልፈጸመ ወይም የሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያውን ከተርሚናል ጋር ሳያያይዝ ከተጠቀመ ወይም የሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያው የምርመራ መዝገብ ከመሣሪያው ጎን እንዲቀመጥ ካላደረገ ወይም በሽያጭ መመዝገቢያ የተመዘገቡ ዕቃዎች ተመላሽ መደረጋቸው ወይም ደንበኛው የተመላሽ ጥያቄ ማቅረቡ በተመላሽ መዝገብ ላይ በትክክል መመዝገቡ ሳይረጋገጥ የተመላሽ ደረሰኝ ከሰጠ ብር ፳፭ሺ ይቀጣል፣
፮/ የሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያው በስርቆት ወይም ከአቅም በላይ በሆነ ምክንያት ጉዳት የደረሰበት በመሆኑ አገልግሎት መስጠት ሲያቋርጥ በሦስት ቀናት ጊዜ ውስጥ ወይም በሌላ ማናቸውም ምክንያት የሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያው ብልሽት ባጋጠመው በሁለት ሰዓት ውስጥ ለአገልግሎት ማዕከሉና ለባለሥልጣኑ ካላስታወቀ ብር ፹ሺ ይቀጣል፣
፯/ የሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያ የሚቀመጥበትን የንግድ ቦታ ትክክለኛ አድራሻ ለባለሥልጣኑ ያላስታወቀ እንደሆነ ብር ፶ሺ ይቀጣል፣
፰/ የአድራሻ ወይም የስም ለውጥ ሲያደርግ ወይም የንግድ ሥራውን የሚያቋርጥ ሲሆን ከሦስት ቀናት አስቀድሞ ለአገልግሎት ማዕከሉና ለባለሥልጣኑ ያላስታወቀ እንደሆነ ብር ፳፭ሺ ይቀጣል፣
፱/ የሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያው ጥቅም ላይ በሚውልበት የንግድ ሥራ ቦታው፣
ሀ/ የተጠቃሚውን ስም፣ የንግድ ስም፣ የንግዱ ሥራ የሚካሄድበትን አድራሻ፣ የታክስ ከፋይ መለያ ቁጥር፣ የሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያውን የዕውቅና እና የመጠቀሚያ ፈቃድ ቁጥር፣
ለ/ ‹‹የሽያጭ ሠራተኞች መሣሪያው የተበላሸ ከሆነ በባለሥልጣኑ ፈቃድ የታተመ ተከታታይ ቁጥር ያለው ደረሰኝ ለደንበኛው የመስጠት ግዴታ አለባቸው›› የሚል ማስታወቂያ፣ እና
ሐ/ ‹‹ደረሰኝ የማይሰጥ ከሆነ አይክፈሉ›› የሚል ጽሑፍ ያለበት ማስታወቂያ፣ በግልጽና በሚታይ ቦታ ለጥፎ ካልተገኘ ብር ፲ሺ ይቀጣል፣
፲/ ሥራ ላይ የዋለውን የሽያጭ ነቁጣ ሶፍት ዌር ባለሥልጣኑ ዕውቅና ባልሰጠው ሰው እንዲቀየር ወይም እንዲሻሻል ካደረገ ብር ፴ሺ ይቀጣል፡፡

፵፯ለየአቅራቢነትግዴታዎችንባለመወጣትየሚጣልመቀጫ
ማንኛውም የሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያዎች ወይም ሶፍትዌር አቅራቢነት ዕውቅናና ፈቃድ የተሰጠው ሰው፣
፩/ የንግድ ሥራውን የአድራሻ ለውጥ ለባለሥልጣኑ ካላስታወቀ ብር ፩፻ሺ ይቀጣል፣
፪/ በባለሥልጣኑ ዕውቅና ያልተሰጠውን የሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያ ለገበያ ካዋለ ብር ፭፻ሺ ይቀጣል፣
፫/ ለእያንዳንዱ የሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያ ምዝገባ ከባለሥልጣኑ የመሣሪያ መለያ ቁጥር ካልወሰደ ወይም የወሰደውን የመሣሪያ መለያ ቁጥር ለእይታ በሚያመች ቦታ በመሣሪያው ላይ ካልለጠፈ ብር ፶ሺ ይቀጣል፣
፬/ በሥራ ላይ ባሉ የሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያዎች ላይ የሚያደርገውን ማናቸውም ለውጥ ለባለሥልጣኑ በቅድሚያ ካላስታወቀ ወይም ስለ መሣሪያው አጠቃቀም በሚያብራራው የአጠቃቀም መመሪያ ውስጥ ትክክለኛ ያልሆነ መረጃ ካስገባ ወይም ትክክለኛውን መረጃ ከቀነሰ ብር ፩፻ሺ ይቀጣል፣
፭/ የሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያዎች በመሰረቃቸው ወይም ሊጠገኑ በማይቻልበት ሁኔታ በአደጋ ምክንያት ብልሽት የደረሰባቸው መሆኑን አስታውቀው እንዲተኩላቸው ለሚጠይቁ የአገልግሎት ማዕከላት በሦስት ቀናት ውስጥ ለማቅረብ አለመቻሉን ለባለ ሥልጣኑ አስቀድሞ ካላስታወቀ ብር ፶ሺ ይቀጣል፣
፮/ ውል ስለተዋዋላቸው የአገልግሎት ማዕከላት መረጃ ካልያዘ ወይም ውላቸውን ስላቋረጡ ወይም አዲስ ስለተዋዋላቸው የአገልግሎት ማዕከላት ለባለሥልጣኑ ካላስታወቀ ብር ፶ሺ ይቀጣል፣

፵፯ሐየአገልግሎትማዕከልግዴታዎችን ባለመወጣትየሚጣልመቀጫ
ማናቸውም የሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያዎች የአገልግሎት ማዕከል፣
፩/ የሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያ የፊሲካል ማስታወሻ በተተካ በሁለት ቀናት ውስጥ ለባለሥልጣኑ ካላስታወቀ ብር ፳ሺ ይቀጣል፣
፪/ ውል የገባባቸውን የሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያዎች በዓመት አንድ ጊዜ የቴክኒክ ምርመራ ካላደረገ ብር ፳ሺ ይቀጣል፣
፫/ አቅራቢው ዕውቅና ሳይሰጠውና በባለሥልጣኑ ዘንድ ሳይመዘገብ በሥራ ላሰማራው ለእያንዳንዱ ሠራተኛ ብር ፶ሺ ይቀጣል፡፡››
፲፱/ ከአዋጁ አንቀጽ ፶ ቀጥሎ የሚከተሉት አዲስ አንቀጽ ፶ሀ፣ ፶ለ፣ ፶ሐ፣ ፶መ፣ ፶ሠ፣ እና ፶ረ፣ ተጨምረዋል፣

‹‹፶ሀ. ለተጨማሪእሴትታክስከፋይነትአለመመዝገብ
ለተጨማሪ እሴት ታክስ ከፋይነት የመመዝገብ ግዴታ ያለበት ሆኖ ሳይመዘገብ የተገኘ ግብር ከፋይ ጥፋተኝነቱ በፍርድ ቤት ሲረጋገጥ ከብር ፲ሺ እስከ ብር ፶ሺ በሚደርስ የገንዘብ መቀጫና ከአንድ እስከ ሁለት ዓመት በሚደርስ እሥራት ይቀጣል፡፡
፶ለ. የተጨማሪ እሴት ታክስ ባልሆነ ደረሰኝ
ወይም ያለደረሰኝ ግብይት ማካሄድ
፩/ ማንኛውም ለተጨማሪ እሴት ታክስ የተመዘገበ ሰው ያለተጨማሪ እሴት ታክስ ደረሰኝ ግብይት ሲያካሂድ ከተገኘ ጥፋተኝነቱ በፍርድ ቤት ሲረጋገጥ ከብር ፲ሺ በማያንስ እና ከብር ፩፻ሺ በማይበልጥ የገንዘብ መቀጫ እና ከሁለት እስከ አምስት ዓመት በሚደርስ እሥራት ይቀጣል፡፡
፪/ በዚህ አንቀጽ ንዑስ አንቀጽ /፩/ በተጠቀሰው ሕገወጥ ደረሰኝ ላይ በተመለከተው የገንዘብ መጠን መሠረት መከፈል የነበረበት ታክስ ከብር ፩፻ሺ በላይ ከሆነ የሚጣለው የገንዘብ ቅጣት የታክሱን መጠን ያህል ይሆናል፡፡

፶ሐ. ያልተፈቀደደረሰኝመጠቀምወይምማተም
ከባለሥልጣኑ ፈቃድ ሳይሰጥ በኮምፒውተር የተዘጋጀ ደረሰኝ ወይም ደረሰኝ በማሳተም የተጠቀመ ወይም የደረሰኝ ሕትመት አገልግሎት የሰጠ ሰው ጥፋተኝነቱ በፍርድ ቤት ሲረጋገጥ ከብር ፲ሺ እስከ ብር ፩፻ሺ በሚደርስ የገንዘብ መቀጫና ከሁለት እስከ አምስት ዓመት በሚደርስ እሥራት ያስቀጣል፡፡

፶መ. የሽያጭመመዝገቢያመሣሪያአጠቃቀምን በሚመለከትስለሚፈጸምጥፋት
ማንኛውም በሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያ የመጠቀም ግዴታ ያለበት ሰው፡-
፩/ በባለሥልጣኑ ዕውቅና ያልተሰጠው ወይም ያልተመዘገበ የሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያ ከተጠቀመ ጥፋተኛ መሆኑ በፍርድ ቤት ሲረጋገጥ ከአንድ ዓመት በማያንስና ከሁለት ዓመት በማይበልጥ እሥራት ይቀጣል፣
፪/ መሣሪያው በጥገና ላይ ባለበት ጊዜ ካልሆነ በስተቀር በሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያ ከታተመ ደረሰኝ ውጪ ወይም ያለደረሰኝ ግብይት ካከናወነ ጥፋተኛ መሆኑ በፍርድ ቤት ሲረጋገጥ ከአንድ ዓመት በማያንስና ከሁለት ዓመት በማይበልጥ እሥራት ይቀጣል፣
፫/ በሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያው የፊሲካል ማስታወሻ ላይ ጉዳት ያደረሰ ወይም የፊሲካል ማስታወሻው እንዲቀየር ያደረገ ወይም ጉዳት ለማድረስ ወይም ማስታወሻውን ለመቀየር ሙከራ ያደረገ ከሆነ ጥፋተኛ መሆኑ በፍርድ ቤት ሲረጋገጥ ከሦስት ዓመት በማያንስና ከአምስት ዓመት በማይበልጥ እሥራት ይቀጣል፣
፬/ የባለሥልጣኑ ሠራተኛ የሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያውን ሥርዓት ኦዲት እንዳያደርግ መሰናክል የፈጠረ ወይም በመሣሪያው ላይ በዓመት አንድ ጊዜ በአገልግሎት ማዕከል የቴክኒክ ምርመራ ያላስደረገ ከሆነ ጥፋተኛ መሆኑ በፍርድ ቤት ሲረጋገጥ ከስድስት ወር በማያንስና ከአንድ ዓመት በማይበልጥ እሥራት ይቀጣል፣
፭/ የሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያው የሚገኝበትን የንግድ ቦታ ትክክለኛ አድራሻ ለባለሥልጣኑ ያላስታወቀ እንደሆነ ጥፋተኛ መሆኑ በፍርድ ቤት ሲረጋገጥ ከስድስት ወር በማያንስና ከአንድ ዓመት በማይበልጥ እሥራት ይቀጣል፡፡

፶ሠ. በአቅራቢያዎችየሚፈጸሙጥፋቶች
ማንኛውም በሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያዎች ወይም ሶፍትዌር አቅራቢነት ዕውቅናና ፈቃድ የተሰጠው ሰው፡-
፩/ የንግድ ሥራውን የአድራሻ ለውጥ ለባለሥልጣኑ ካላስታወቀ ጥፋተኛ መሆኑ በፍርድ ቤት ሲረጋገጥ ከአንድ ዓመት በማያንስና ከሁለት ዓመት በማይበልጥ እሥራት ይቀጣል፣
፪/ በባለሥልጣኑ ዕውቅና ያልተሰጠውን መሣሪያ ለገበያ ካዋለ ጥፋተኛ መሆኑ በፍርድ ቤት ሲረጋገጥ ከሦስት ዓመት በማያንስና ከአምስት ዓመት በማይበልጥ እሥራት ይቀጣል፣
፫/ በሥራ ላይ ባሉ የሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያዎች ላይ የሚያደርገውን ማናቸውም ለውጥ ለባለሥልጣኑ በቅድሚያ ካላስታወቀ ወይም በመሣሪያው የአጠቃቀም መመሪያ ውስጥ ትክክለኛ ያልሆነ መረጃ ካስገባ ወይም ትክክለኛውን መረጃ ከቀነሰ ጥፋተኛ መሆኑ በፍርድ ቤት ሲረጋገጥ ከሦስት ዓመት በማያንስና ከአምስት ዓመት በማይበልጥ እሥራት ይቀጣል፡፡

፶ረ. በሽያጭመመዝገቢያመሣሪያዎች የአገልግሎትማዕከልናሠራተኞችየሚፈጸሙጥፋቶች
፩/ ማናቸውም የሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያዎች የአገልግሎት ማዕከል አቅራቢው ዕውቅና ያልሰጠውንና በባለሥልጣኑ ዘንድ ያልተመዘገበ ሠራተኛ በሥራ ላይ አሰማርቶ ከተገኘ ጥፋተኛ መሆኑ በፍርድ ቤት ሲረጋገጥ ከአንድ ዓመት በማያንስና ከሦስት ዓመት በማይበልጥ እሥራት ይቀጣል፡፡
፪/ ማናቸውም የሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያዎች የአገልግሎት ማዕከል ሠራተኛ የሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያን ያለአገልግሎት ማዕከሉና ያለባለሥልጣኑ ዕውቅና ከፈታታ ወይም ከገጣጠመ ወይም የሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያ ሳይበላሽ ሆን ብሎ እሽጉን ካነሳ ወይም አካሉን ከቀየረ ወይም እነዚህን የመሳሰሉ አድራጎቶች ከፈጸመ ጥፋተኛ መሆኑ በፍርድ ቤት ሲረጋገጥ ከብር ፭ሺ በማይበልጥ የገንዘብ መቀጫ እና ከአንድ ዓመት በማያንስና ከሦስት ዓመት በማይበልጥ እሥራት ይቀጣል፡፡››
፳/ በአዋጁ አንቀጽ ፶፩ ንዑስ አንቀጽ /፩/ ውስጥ ‹‹በ፪ /ሁለት/ ዓመት እስራት›› የሚለው ሐረግ ተሰርዞ ‹‹ከአንድ ዓመት በማያንስና ከሁለት ዓመት በማያንስና ከሁለት ዓመት በማይበልጥ እሥራት›› በሚለው ተተክቷል፡፡
፳፩/ የአዋጁ አንቀጽ ፶፫ ንዑስ አንቀጽ /፪/ እና /፫/ የነበሩት ንዑስ አንቀጽ /፬/ እና /፭/ ሆነው የሚከተሉት አዲስ ንዑስ አንቀጽ /፪/ እና /፫/ ተጨምረዋል፣
‹‹፪/ የባለሥልጣኑ ሠራተኛ የሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያዎች አጠቃቀም ደንብና መመሪያዎችን በመተላለፍ፣
ሀ/ የሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያ የፈታታ ወይም የገጣጠመ ወይም የሰርቪስ ሠራተኛ በሌለበት ሥራ ላይ እንዲውል የፈቀደ ወይም የመሣሪያውን መለያ ቁጥር ያቀያየረ እንደሆነ፣ ወይም
ለ/ በሽያጭ መመዝገቢያ መሣሪያ ተጠቃሚው ወይም በአገልግሎት ማዕከሉ ወይም በሠራተኛው ወይም በአቅራቢው የተፈጸመን ማናቸውንም ሕገ ወጥ አድራጎት እያወቀ ወይም በቸልተኝነት በ፳፬ ሰዓት ጊዜ ውስጥ ለባለሥልጣኑ ሪፖርት ያላደረገ እንደሆነ፣
ጥፋተኛ መሆኑ በፍርድ ቤት ሲረጋገጥ ከብር ፭ሺ በማያንስና ከብር ፲ሺ በማይበልጥ የገንዘብ መቀጫ እና ከአንድ ዓመት በማያንስና ከሦስት ዓመት በማይበልጥ እሥራት ይቀጣል፡፡
፫/ የግብር ባለሥልጣኑ ሠራተኛ ያለ በቂ ምክንያት ጉዳይን በማጓተት በግብር ከፋይ ላይ ለሚያደርሰው ጉዳት በፍትሐ ብሔር ያለበት ኃላፊነት እንደተጠበቀ ሆኖ ጥፋተኛነቱ በፍርድ ቤት ሲረጋገጥ ከአንድ ዓመት በማያንስና ከሁለት ዓመት በማይበልጥ እሥራት ይቀጣል፡፡››

. አዋጁየሚፀናበትጊዜ
ይህ አዋጅ በፌዴራል ነጋሪት ጋዜጣ ታትሞ ከወጣበት ቀን ጀምሮ የፀና ይሆናል፡፡

አዲስ አበባ ታህሣሥ ፲፮ ቀን ፪ሺ፩ ዓ.ም.
ግርማ ወልደጊዮርጊስ
የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ  ሪፐብሊክ ፕሬዚዳንት

ጠጥቶ ፈረስ መንዳት

ጠጥቶ መንዳት ክልክል ነው፡፡ ይህን ህግ ጠጥተው የማውቁ ሆነ ነድተው የማውቁ ሁሉ ያውቁታል፡፡ ግን ምን መንዳት ነው የተከለከለው? ለምሳሌ የሚነዳው መኪና መሆኑ ቀርቶ ፈረስ ቢሆንስ? በአሜሪካ ፔንስላቫኒያ ግዛት ፍርድ ቤት በቀረበ ጉዳይ ላይ ይኸው ነጥብ ሁሉንም ዳኞች ባያስማማም ፈረስም፤ መኪናም ያው ነው የሚል አቋም ተይዞ ፍርድ ተሰጥቷል፡፡ (Pennsylvania v. Noel, 857 A.2d 1283 (Pa. 2004) (Eakin, J., dissenting). ) ፍርዱ የተሰጠው እንደሚከተለው በግጥም ነበር፡፡

A horse is a horse, of course, of course,
but the Vehicle Code does not divorce
its application from, perforce,
a steed, as my colleagues said.
“It’s not vague” I’ll say until I’m hoarse,
and whether a car, a truck or horse
this law applies with equal force,
and I’d reverse instead.